Wednesday, December 4, 2013

ሰበር ዜና - የመስቀል ክብረ በዓል የዓለም ቅርስ ሆነ


Ethiopian Reporter 
የኢትዮጵያው የመስቀል ክብረ በዓል በዓለም ቅርስነት መመዝገቡን ዩኔስኮ አስታወቀ፡፡ ዩኔስኮ የመስቀል ክብረ በዓልን (Commemoration feast of the finding of the True Holy Cross of Christ)

በዓለም ቅርስነት መመዝገቡን ኅዳር 25 ቀን ይፋ ያደረገው፣ በኢንታንጀብል (መንፈሳዊ) ባህላዊ ቅርሶች ጥበቃና ክብካቤ ላይ የሚሠራው ኮሚቴው ስምንተኛውን ጉባኤ እያካሄደባት ካለው የአዘርባጃኗ  ባኩ ከተማ ነው፡፡

ስለቅርሱ የመረመረው ኮሚቴ ባቀረበው ውሳኔ ሐሳብ ላይ እንደተመለከተው፣  የመስቀል ክብረ በዓል የኢትዮጵያን ሃይማኖታዊና ባህላዊ ትውፊቶችን የያዘ፣ ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲተላለፍ መምጣቱና በአገሪቱ ማኅበራዊ አንድነትንና የርስ በርስ ትስስርን፣ ብዝኃነትንም የሚያንፀባርቅ፣ በበርካታ ብሔረሰቦች ባህሎች መካከል ትስስርን የፈጠረ በመሆኑ ዓለም አቀፍ መስፈርቱን አሟልቷል ብሎታል፡፡



የዩኔስኮ ኮሚቴው በረቡዕ ስብሰባ ውሎው  ከመስቀል ሌላ ከተለያዩ አገሮች 13 መንፈሳዊ ባህላዊ ቅርሶችን በሰው ዘር ቅርስነት መመዝገቡንም በድረ ገጹ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
መስቀልን ጨምሮ እ.ኤ.አ. በ2013 የተመረጡትን የ14ቱ መንፈሳዊ
ባህላዊ ቅርሶች ገጽታ የሚያሳዩ ቪዲዮዎችና ፎቶዎችም በዕለቱ በድረ ገጹ ላይ መለቀቃቸው ታውቋል፡፡

በየዓመቱ መስከረም 17 ቀን በመላ አገሪቱ በአደባባይ ደመራ የሚከበረው የመስቀል ክብረ በዓል የመጀመርያው መንፈሳዊ (ኢንታንጅብል) ባህላዊ ቅርስ ሆኖ በዩኔስኮ የተመዘገበላት ኢትዮጵያ፣  ዘጠኝ  ግዙፍ (ታንጀብል) ቅርሶች ማስመዝገቧ ይታወቃል፡፡
http://www.ethiopianreporter.com

No comments:

Post a Comment