Sunday, September 11, 2011

‹‹ሕዝቡና መንግሥት ተረባርበው አንድ አቋም ካልወሰዱ እንኳን ወርቅ ለማግኘት ነሐስም ያሰጋኛል›› ዶ/ር ወልደመስቀል ኮስትሬ


ሪፖርተር ጋዜጣ

የቀድሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ አትሌቲክስ ቡድን ዋና አሠልጣኝ
በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ወቅታዊ ሁኔታ ዙርያ ከቀድሞው የኢትዮጵያ ብሔራዊ አትሌቲክስ ቡድን ዋና አሠልጣኝ ዶ/ር ወልደመስቀል ኮስትሬ ጋር ሔኖክ ያሬድ ቆይታ አድርጓል፡፡

ሪፖርተር፡- መሰንበቻውን የዴጉን 13ኛ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ተመልክተናል፡፡ የኢትዮጵያንም ውጤት አይተናል፡፡ ግምገማዎ ምንድን ነው?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- ከአንድ ውድድር በኋላ ምንጊዜም ቢሆን የአገሪቱ ስፖርት ምን ደረጃ ላይ እንዳለ ለመገምገም የሚያበቃው የሥራ ውጤት ነው፡፡ እንደ ኃላፊነት ሳይሆን እንደባለሙያ በግሌ የምሰጠው አስተያየት አለ፡፡ ለዓለም ሻምፒዮናው ምን ያህል ተዘጋጅተናል? ምን ያህልስ አስበንበታል? ከሚለው ነው መነሣት አለብን፡፡
ለዚህ ዝግጅት ምን ወጪ አውጥተናል? ስንት ሰው አቅፈን በዝግጅት አቆይተናል? ብቃት አላቸው ብለን ያመንባቸውን ስፖርተኞችስ አዘጋጅተን ልከናል የሚለው የሚታይ ነው፡፡ ውጤቱ ምንም አይደለም፤ ስፖርት በመሠረት ተሳትፎ ቢሆንም የዓለም ሻምፒዮናው ግን የተሳትፎ ውድድር ሳይሆን የውጤት ውድድር ነው፡፡
ባለፈው ሁለት ዓመት ምን አመጣን? በኦሊምፒክስ ምን አመጣን?  ከ20 ዓመት ወዲህ ጀምረን ያበረከትናቸው ውጤቶች ምን ይመስላሉም ይታያል፡፡  ከተሳትፎ ባሻገር ውጤት የምናስመዝግብበት ነው፡፡ ውጤት ሊወጣ ሊወርድ ይችላል፡፡ ውጤት ሲመጣ ደስ ይላል፡፡ ለእኛ ብቻ ሳይሆን ለአኅጉራችን አፍሪካም ጭምር ነው፡፡ በእኛና በኬንያ መካከል ያለችው ልዩነት በጣም ትንሽ ነች፤ በአንድ በተወሰነ መስክ እናሸንፋቸዋለን፡፡ ግን ከዚህ ዓመት ቀደም ብሎ አካሔዱ ጥሩ አልነበረም፡፡
የነበረን አለመግባባት የእኛ ውጤቱ ብቻ ሳይሆን አካሔዱም መስተካከል አለበት ነው፡፡ እኛ በአሁኑ ጊዜ የሰው አገር ኤክስፐርት ብዙም የሚያስፈልገን አልነበረም፡፡ ብዙ ጊዜ ራሳችንን ችለናል፡፡ ሌሎች አፍሪካውያንና አውሮፓውያን ዝንባሌያቸውና ትኩረታቸው ወደኛ ነው፡፡ እንዴት ነው የሚያሸንፉን የሚለው ጥያቄ ውስጥ ገብተዋል፡፡ የዚያ ሁሉ ባለቤትና ባለድል ሆነን እያለን የነበረውን የአካሔድ አሠራር ትተን ዴሞክራሲ በግል በሚለው አስተያየት ላይ አዘነበልን፡፡ ኧረ ይኼ ነገር አያዋጣንም፡፡ አንደኛ በቂ ሜዳ፣ በቂ ገንዘብ፣ በቂ የሰው ኃይል የለንም፡፡
የእኛ የሰው ኃይላችን አትሌቶቹ ናቸው፡፡ ከዚያ ውስጥ እየመለመልን እያወጣን ለውጤት እናብቃ ብንል አይጎዳንም፤ የልጆቹንም ዴሞክራሲ መከልከል ነው አሉ፡፡ የልጆቹ ዴሞክራሲ ልምምድ ማድረግ ውጤት ማምጣት፤ በውጤታቸውም መጠቀም ነው፡፡ ጥቅሙ ለፌዴሬሽኑም ለአገርም ነው፡፡ ለልጆቹም ለእኛም ጭምር ነው፡፡ የለም እንደፈለጉ ይሁኑ፤ አንይዝም አሉ ተበታተኑ፡፡

ሲበታተኑ ትንሽ ብቃቱና የውጭ ግንዛቤ ያላቸው ተጠቃሚ ናቸው፡፡ ግን እነሱ ሲጠቀሙ ደግሞ ታዳጊዎቹ ተተኪዎቹ ደግሞ ከነርሱ መማር አለባቸው፡፡ በጭፍን አይደለም ሁሉ ነገር እጃችን ላይ ነው ያለው ሲስተማችንም ነው፡፡ በዓለም ሻምፒዮና ዝግጅት ላይ ጭቅጭቅ ነበር፡፡ ግማሹ በግሉ ይሠራል፤ ግማሹም አይመጣም፡፡ ቁጥጥሩም እስከዚህ አይደለም፤ ማነው ኃላፊ ቢባል ሁሉም በጋራ ፌዴሬሽኑ ነው ይባላል፡፡ ሥራ አስኪያጅ ኮሚቴ ነው? ቴክኒክ ክፍል ነው? አሠልጣኙ ነው? ማን ነው? ልዩነት የለም፡፡ ውጤቱም ታየ፡፡

በ20 ዓመት ውስጥ ከ20 ያልበለጡ ሜዳሊያዎች ሰብስበናል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ከፍና ዝቅ ማለቱ ያለ ነገር ነው፡፡ የልጆቹ ብዙ አለመዘጋጀትና የግል አመለካከት በውጤቱ ላይ ተፅዕኖ ፈጥሯል፡፡ በመጨረሻው ዴሞክራሲ ከተባለ በኋላ ማንም በጋራ የሚሠራ የለም፡፡ ማን ተቀዳሚ ማን ተከታይ የሚለው ነገርም የለም፡፡ ትልቁ ስንጠቀምበት የነበረው የቡድን ሥራ ነበር፡፡ ለምን ታስገድዳቸዋለህ የሚል ነገር መጣ፤ አይደለም ማስገደድ ሳይሆን ለአገር ነው፡፡ ወታደርና ስፖርተኛ አንድ ነው፡፡
ሁለቱም የሚሔዱት ለማሸነፍ ነው፡፡ ማናጀሮች የሚባሉት የፈረንጅ ደላሎች የሚፈልጉት መገንጠል ነበር፤ በዚያ ተሳካላቸው በቁጥጥራቸው ሥር አዋሉት፡፡ በኮሮስፖንዳንስ (በመላላክ) ከውጪ እንዲህ ሥራ ማለት አመጡ፡፡ ማን ነው መመርያ የሚሰጠን? የትኛው ፈረንጅ ነው ለአገሩ ሠርቶ ውጤት ያመጣው? ይኼ’ኮ የጥቁር ገበያ ነው፤ እኛን ከነፃነት ወደ ቅኝነት (ኮሌኒ) እየወሰዱን ነው፡፡ በእነርሱ እንድንተማመን እያደረጉ ነው፤ ለምንድን ነው ስንል ዝም ብለው ነው የሚል አባባል መጣና እዚህ ደረስን፡፡ ለማንኛውም አሁን ለንደን ኦሊምፒክ ከፊታችን ነው፡፡ ምንድን ነው የምንሠራው? ከየት ነው የምንነሣው? እነማንን ይዘን ነው? አብዛኛዎቹ ልጆቻችን ዕድሜያቸው እየገፋ ነው፡፡ በድግግሞሽ ልምዳቸው እየተቀነሰ ነው፡፡ ምንድን ነው የምናደርገው ወቅታዊ የሆነ አስተያየት መስጫና መዘጋጃም ነው፡፡ በዚህ በዘጠኝ ወር ውስጥ ምን እንዴት ነው የምንሠራው? ማየት አለብን፡፡ ኦሊምፒክ ቀላል ነገር አይደለምና፡፡ 

ሪፖርተር፡- ከዚህ በፊት ብሔራዊ ቡድኑ አንድ ላይ ይሰባሰብ ነበር፡፡ በዋናው አሠልጣኝ መሪነት ቴክኒካል ስታፍ የነበረበት አካሔድ ነበረው፡፡ አሁንስ ያ ሥርዓት አለ?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- የለም፡፡ ብሔራዊ ቡድኑ ፈርሶ ውድድር ሲደርስ ከየክለቡ ከዚህም ከዚያም መርጦ ያወዳድራል፡፡ ምን ደረጃ ላይ እንዳሉ፣ ምን ችሎታና ፔስ እንዳላቸው አይታወቅም፡፡ አንድ ወር ሲቀር ኑ አሏቸው፡፡ አብዛኞቹ መጡ፤ ሌሎቹም እምቢ አሉ፡፡ እንደ ኃይሌ ገ/ሥላሴ ዓይነት አልመጣም፤ አልተሳተፈም፡፡ የዓለም ማራቶን ሪከርድ የያዘው እርሱ ቢሆንም በዚህ ውድድር ላይ አልተካፈለም፤ ያስገደደው ሁኔታ የለም፡፡ እርግጥ ስፖርት በፈቃደኝነት የሚሠራ ነገር ነው፡፡ ግን አገር የሚወክል ደግሞ ኃላፊነቱ የአገር ነው፤ የመንግሥት፣ የሕዝብም፣ የፌዴሬሽንም ነው፡፡ ይኼ ተግባር አልተከናወነም፡፡ በዚሁ ከሔድን ደግሞ ለነገው ወዴት ነው የምንሔደው የሚለው ጥያቄ በጣም በጣም መንግሥትንም ሕዝብንም አጠያያቂ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- ኬንያውያኑ በዴጉ የበላይነቱን እንዴት ነው የወሰዱብን?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- እነርሱ የወሰዱት የእኛን ሲስተም ነው፡፡ አሠለጣጠኑንም ቁጥጥሩንም እንዳለ የእኛን ወሰዱ፡፡ እኛ ደግሞ የእነርሱ የነበረውን እንደፈለጋችሁ ሁኑ የሚለውን ወሰድን፡፡ እንደፈለጋቸው ይሮጣሉ መቼ ነው ቤዚክ ኢንዱራንስ የሚሠሩት? መቼ ነው ስፔሲፊክ ኢንዱራንስ የሚሰጡት? መቼ ነው ውድድር ተኮር ልምምድ የሚያደርጉት የሚለው ነገር የለም፡፡ ያንን ነው ያጣነው፡፡ ለምንድን ነው ይኼ የተደረገው ስንል ምላሹ በቃ ዴሞክራሲ የሚል ነው፡፡

ሪፖርተር፡- ውድድሩን ስንመለከት በወንዶቹም በሴቶቹም ያ የምንታወቅበት የቡድን ስሜት አልተንፀባረቀም፡፡ አንዳንዶቹ እንደሚሉት፣ አሠልጣኞቹ በቅጡ የሚያውቋቸው አይመስሉም?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- ተወዳዳሪዎቹን ያመጧቸው ከየክለቡ ነው፡፡ ሁለተኛ ነገር ዕውቀቱ ሊኖራቸው ይችላል፤ ብዙዎቹ አላቸው፡፡ ከእኛም ጋር ብዙ ጊዜ ቆይተዋል፡፡ የአስተዳደሩ ሁኔታ ግን አስቸጋሪ ነው፡፡ ልጆቹን አይመሯቸውም፡፡ መሪዎቹ ልጆቹ ናቸው፡፡ በጣም ያከብሯቸዋል፡፡ አሠልጣኝና አትሌት መከባበራቸው ጥሩ ነው፡፡ ግን የተገላቢጦሽ ነው፡፡ መጀመሪያ ነገር መምራት ያለበት አሠልጣኙ እንጂ ተወዳዳሪው መሆን የለበትም፡፡ የአንድ አሠልጣኝ ቃል መከበር አለበት፡፡ ሥርዓታዊ መሆን ያስፈልጋል፡፡ ትልቁ ውድቀታችን እርሱ ነው፡፡ እንደ ባለሙያ አስተያየት እንዳይደገም እላለሁ፡፡ ኮንትሮል መደረግ አለባቸው፡፡ ሲወዳደሩኮ የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማና መዝሙር ይዘው ነው፡፡  ያ ደግሞ የአገርም የመንግሥትም ጉዳይ ነው፡፡ ካሁኑ እንንቃ፡፡ መሻኮቱን ተወውና ሙያዊ አስተያየት ለመስጠት እፈልጋለሁ፡፡ አሁን ወድቀናል፡፡ አሁን ስናየው ተተኪ የለንም፤ በፊትም ሥጋቱ ቢኖረንም አንድ ውድድር ሲመጣ ማን ማን እንደሚወክል እንዘጋጃለን፡፡ እነ ኃይሌን የተኩት እነ ቀነኒሳ ናቸው፡፡ እነ ኃይሌ እነ ፊጣን ነው የተከተሉት፡፡ ይኸ የክትትል አሠራር ሥርዓት (ሲስተማችን) ሁሉ ቀርቷል፡፡ የሲስተም ድሀ አይደለንም፡፡ ወጣቶች ሞልተዋል፤ ትንሽ መያዝና ተቆጣጥሮ ማሠልጠን ብቻ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- በሻምፒዮናው እንዳየነው ጤናቸው ያልተሟላን አትሌቶችን ማሳተፍ ተገቢ ነው?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- በምንም ነገር አንድ አትሌት የሚዘጋጀው ለዚያ ውድድር ይደርሳል ተብሎ ነው፡፡ የታመሙ ከሆኑ እክል ከደረሰባቸው ወደ ሕክምና ነው የሚሔዱት፤ ጤና ሆነው እስከሚገኙና ልምምድ መሸፈን እስከሚችሉ ይጠበቃሉ፡፡ አሁን እኮ ልምምድ የሚሸፍን የለም፤ አሞኛል ይላል፤ ወይ ለራሱ ኮተቤ ወይም እንጦጦ ይሔዳል፡፡ ያ የቁጥጥር ሥርዓታችን ደክሟል፤ ይኼ መጥበቅ አለበት፡፡ ግዴታ አይደለም የውዴታ ግዴታ ነው፡፡ የአገር ግዴታ ነው፡፡ አንድ ወታደር ጦር ሜዳ ሲሔድ ይኼ ይሆነኛል ያ አይሆነኝም አይልም፤ ጦር ሜዳ ነውና፡፡ የስፖርቱ መድረክም የሰላም ጦርነት ነው፡፡ እርግጥ ልጆቹ ይነግዱ፤ ያግኙ፤ አታግኙ አይደለም፤ ጊዜያቸው ዛሬ ነው ደክመው ሜዳ ላይ መውደቅ የለባቸውም፡፡ ለዚያ ተመቻችቶላቸዋል፡፡ ግን ጨርሰው እንዲጠፉ መሆን የለበትም፡፡ ተተኪን እየተኩ መልቀቅ አለባቸው፡፡ ሕዝብም መንግሥትም አገሪቱም ኢንቨስት አድርገውባቸዋል፤ ተተኪ ያስፈልገናል፡፡ ሁልጊዜ ወርቅ የሚያገኝ ይኖራል ማለት አይደለም፡፡ እነ አበበ ቢቂላ ከሔዱ በኋላ እነ ገዛኸኝ መቼ ነው የመጡት? ድካም፣ ልምምድና ቆራጥነት ይጠይቃል፡፡ ሲስተም ይጠይቃል፡፡ አካሔዱ ጥሩ ስላልሆነ ካሁኑ ጋዜጠኛውም፣ ባለሥልጣኑም፣ ባለሙያውም መታገል አለበት፡፡ ካለቀ በኋላ ምክንያት መስጠትና ጣት መቀሳሰር አይደለም፡፡ ከአሁኑ አደራ ማለት ያለብን ለዚህ ነው፡፡ መሸርሸርና መቀነስ የጀመርነው ከ1991 ዓ.ም ጀምሮ ነው፡፡ ሽኩቻ አለ፡፡ በትክክል ያለመሥራት፣ ያለመግባባት አንዱ በአንዱ ላይ ትዕዛዝ የማድረግ፣ ኃይል አለኝ የማለት ንትርክ ከመጣ ስፖርቱ በሰላም አይሔድም፡፡ በአንደኛው ሻምፒዮና አንደኛ የሚሆነው በቀጣዩ በቀጥታ የሚሆነው 4ኛ አትሌት ሆኖ ይገባል፡፡ በሻምፒዮናው በሴቶች አንቀን ስለያዝን ከአንድ እስከ አራት ተከታትለን ገብተናል፡፡ ሠርተን ነው ያገኘነው፡፡ ስለዚህ አንደኛ ውጤት ያለው ሰው መኖር አለበት፡፡ ጀማሪን ብቻ እዚያ አታስቀምጠውም፡፡ አብሮህ ግን ይሆናል፡፡ ይቀስማል፡፡

በፌዴሬሽኑ ደግሞ የሥራ አስኪያጅ ኮሚቴ ሥራውን መሥራት አለበት፡፡ ቴክኒኩ የቴክኒክ ጉዳዩን መከታተል አለበት፡፡ ትልቁ ችግር ጣልቃ ገብነት ነው፤ በፍጹም ይህ መሆን የለበትም፡፡

ሪፖርተር፡- ጣልቃ ገብነቱ ከየት ነው የሚመጣው?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- ለምሳሌ የቴክኒክ ኮሚቴ ወይም አባል የሆነው በአሠልጣኙ ሥራ ለመግባት ይሞክራል፡፡ እኔ ፕላኔን ሰጥቻለሁ፡፡ በዚህ ውጤት ካላመጣሁ እየጠየቅበታለሁ፡፡ ጣልቃ አትግቡ ነው፡፡ ሥራ አስኪያጅ ኮሚቴ የሥራውን ድርሻ ይሥራ፡፡ በሳምንት አንድ ቀን መሰብሰብ አለበት፡፡ አይሰበሰብም፤ ክትትልም የለም፡፡ ክትትል መኖር አለበት፡፡ የሥራ አስኪያጅ ኮሚቴ አባልነትም የዘላለም መሆን የለበትም፡፡ ለአንድ ጊዜ ለአራት ዓመት ይመረጣል፡፡ ሁለተኛ ሊመረጥ ይችላል፡፡ 16 ዓመት ሙሉ በሥራ አስኪያጅ ኮሚቴ አባልነት የተቀመጡ እንደርስት አድርገውታል፡፡ መሆን የለበትም፡፡ ልምዱም ያን ያህል አይደለም፡፡ ፈላጭ ቆራጭነትም መኖር የለበትም፡፡ የሙያ አቅም የላቸውም፡፡ የገቡት ከየክልል በኮታ በመሆኑ በየጊዜው የሚመረጡት እነርሱ ናቸው፡፡ ለምን እንዲህ ይሆናል? ምንድን ናቸው?

ሪፖርተር፡- ክለቦችስ የራሳቸው ተወካይ አላቸው?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- የላቸውም፡፡ እሱ ላይ ጭቅጭቅ አለ፡፡

ሪፖርተር፡- ለምሳሌ አዲስ አበባን ብናይ ብዙ ክለቦች ያሉት እዚህ ነው፡፡

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- የለም፤ ደንቡም የለም፡፡

ሪፖርተር፡-  ከኢንተርናሽናል ፌዴሬሽንም ሆነ ከጎረቤት ኬንያ ተሞክሮ ሲታይ የፌዴሬሽኑ አደረጃጀት እንዴት ነው?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- እንለውጣለን ይላሉ፤ ግን እነዚያ ሰዎች አይወጡም፡፡ ቋሚ ናቸው ዕድሜ ልክ ነው፡፡ ከእነአቶ ሙሉጌታ ጋር የነበሩ አሁንም አሉ፡፡ ፌዴሬሽኑን  የሚያዩት እንደ ርስት ነው፡፡ ደግሞስ ዕውቀት አላቸው ወይ? አንዳንዶቹ ሀብታሞች ናቸው፡፡ ለፌዴሬሽኑ የሚያደርጉት አስተዋጽዖ የለም፡፡  የባለቤትነት ሁኔታዎች አሉ፡፡ ፈላጭ ቆራጭ ነኝ የሚል ነገር አላቸው፡፡ መንግሥትም ሁኔታውን አጢኖ ማስወገድ አለበት፡፡

ሪፖርተር፡- በአትሌቲክስ ስመ ጥር የሆንነውን ያህል በዓለም አቀፉ አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበርም ሆነ በአኅጉሪቷ ኮንፌዴሬሽን በአመራር ውስጥ የለንበትም፡፡ በፊት አቶ ታደሰ መለሰ የአፍሪካ ኮንፌዴሬሽን ሥራ አስኪያጅ ኮሚቴ አባል ነበሩ፡፡ አሁን ማንም የለም፡፡ በዴጉ በተካሔደው ጉባዔ ለመመረጥ ሙከራ ተደርጎ ነበር፤ አልተሳካም፡፡

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- አሠራራችን ነዋ፤ ውጤታችን እየወረደ መጣ፡፡ ይኼ የሚያሳየው ከውጤቱ አኳያ ነው፡፡ እዚያ ላይ ከሚቀርቡት ሰዎች የግል አስተዋጽዖ ይታያል፡፡ በፊት አቶ ሙሉጌታ ደርሶ ነበር፡፡ ባለው ሁኔታ ውጭ ሔዶ ቀረ እንጂ እርሱ ጥሩ ተግባር ስለነበረው ታጭቶም ነበር፡፡ ማነው አሁን ካሉት ውስጥ እዚያ የሚገባው? አቶ ዱቤ ነው? ወ/ሮ ብሥራት ናቸው? ያላቸው እንትን [አቅም] እስከዚም ነው በተቻለ መጠን እነርሱ ለመግባት ሞክረው ነበር፡፡

ሪፖርተር፡- እነ ኬንያ ናቸው ወደ አመራሩ የገቡት?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- በሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴም በቴክኒክ ኮሚቴ ውስጥም አሉበት፡፡ ሁሉም ቦታ አሉ፡፡ አንድ ብቻ አይደለም ሁለት ሦስት አሏቸው፡፡ የተመረጡት ካላቸው ሰብዕና (ፐርሰናሊቲ)  ካላቸው ውጤት ነው፡፡ ኬንያ ያልገባ ማን ይገባል? እኛም እኮ በፊት እጩ ነበርን፡፡ ንጉሤ ሮባም እኔም ነበርኩ፡፡ አልቆየንም፤ የራሳችን ሽኩቻና አለመግባባት ቦታ አሳጥቶናል፡፡ ወ/ሮ ብሥራትን በየትኛው ችሎታቸው ይመርጧቸዋል? ዶ/ር አሸብር ወ/ጊዮርጊስ እግር ኳስ ውስጥ አሉበት፤ ሁኔታው ነው የሚያስመርጥህ የግል ችሎታህ ብቻ አይደለም፡፡ ፐርሰናሊቲህም ይታያል፡፡

ሪፖርተር፡- በፊት በነበረው የቴክኒክ ኮሚቴ ሚናዎ ምን ነበር?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- በሙያህ የቴክኒክ ኮሚቴ ሰብሳቢ ስትሆን፣ የሥራ አስኪያጅ ኮሚቴ አባልም ትሆናለህ፡፡ ብሔራዊ አሠልጣኙ እዚያ ውስጥ አለ፡፡ በአሁን ጊዜ እንደዚህ ዓይነት ነገር የለም፡፡ ፈርሷል፡፡ የተወሰኑ ሰዎች ብቻ ይመሩታል፡፡ እዚያ ውስጥ አቶ አማኑኤል አብርሃም፣ ወ/ሮ ብሥራትና አቶ ነጋ ዋነኞቹ ተንቀሳቃሾችና ፈላጭ ቆራጭ ናቸው፡፡ ሌላው ያለው ለስም (ሲምቦል) ነው፡፡ የሚመጣም የማይመጣም አለ፡፡

ሪፖርተር፡- ሥልጠናውን እንዴት ያዩታል? የአሠልጣኞች ስብስብ ሲታይ የመምህራን ስብስብ ነው የሚሉ አሉ፡፡ አስተማሪነትና አሠልጣኝነት እንዴት ሊተሳሰር ይችላል?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- ሙሉ ለሙሉ ልዩነት አለው፡፡ ስታፍ ስታፍ ነው፡፡ አስተማሪም አስተማሪ ነው፡፡ አስተማሪ ማለት አሠልጣኝ ማለት አይደለም፡፡ አሠልጣኝነት ራሱን የቻለ ፕሮፌሽናል የሆነ ምግባርና መስፈርያም አለው፡፡ መጽሐፍ ስላነበበ አሠልጣኝ ይኮናል እንዴ? በንድፈ ሐሳብ ጥሩ ይሆናል፤ ተግባሩ ግን የት አለ? ሰማንያ እጁ ተግባር ሃያ እጅ ንድፈ ሐሳብ ነው፡፡ ይኼ ካልታወቀ ዝም ብሎ ከራባት አስሮና ከሜዳ መጥቶ ና አሠልጥን ብትለው አይሆንም፡፡ የሚቀበልህም አይኖርም፡፡ አካሔዱንም አታውቀውም፡፡ ከልጁ ወይም ከልጅቷ ጋር ጥል ነው፡፡ ይህ በግልጽ መታወቅና መታየት አለበት፡፡ መንግሥት ይኼን እንደ አቋም፣ እንደ መመርያ አድርጎ ሊወስደው ይገባል፡፡ ይኸ ካልሆነ የትኛውም አገር የትም አይደርስም፡፡ ጥሩ አስተማሪዎች፣ የዩኒቨርሲቲ ሌክቸረሮች አሉ፡፡ ግን አሠልጣኞች አይደሉም፡፡ ሥልጠና ራሱን የቻለ ሙያ ነው፡፡ እኔ ላልጽፍ እችላለሁ፡፡ ሥልጠና ግን ከልጅነቴ ጀምሮ እስከ ትምህርት ቤት ፒኤችዲ እስከማገኝ ድረስ አንዱና ዋናው (ሜጀር) ትምህርቴ አትሌቲክስ ነው፡፡ አትሌቲክስ ደግሞ ብዙ ነው፡፡ ውርወራና ዝላይ ላስተምር እችል ይሆናል፡፡ ሥልጠና ግን አልችልም፤ ልዩነት አለው፡፡ መካከለኛና ረዥም ርቀት ከሕይወቴ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ፒኤችዲ ይዘህ ልታስተምር ትችላለህ፤ ስሜቱ ሊገባህ ልታውቀው ይገባል፡፡ ከልምድህ እንዲያው አይተህ ይኸ ይሆናል ልትል ትችላለህ፤ ልምድና ትምህርት አንድ ላይ ከተያያዘ ትልቁ ነገር እርሱ ነው፡፡ እስከ ዕድሜ ልክህ ማሠልጠንም መጠቀምም ትችላለህ፡፡ ከሥራ አስኪያጅ ኮሚቴ አንዱ፣ እርሳቸው አርጅተዋል አሉኝ አሉ፡፡ ጥሩ እንዲያው የበለጠ ብሩህ ሐሳብ ይኖርሃል፤ አታዳላም ማለት ነው፡፡ ሥልጣን ለመያዝ ጉጉት ይኖራል፤ አሁን ግን ትኩረትህ ሥልጠናህ ላይ ይሆናል፡፡

ሪፖርተር፡-  ፌዴሬሽኑ ብዙዎቹን ውጤታማ አሠልጣኞችን በአግባቡ አይዝም ይባላል፡፡ የተገፉ አሉ፡፡ ስፖርት ኮሚሽንስ አያየውም’?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- ሚኒስትሯ ወ/ሮ አስቴር ማሞ ይከታተሉን ነበር፡፡ በቀጥታ ከቢሯቸው ጠርተው ያነጋግሩን ነበር፡፡ ራዕይ ነበራቸው፡፡ ሌሎቹ እስከዚህም አይደሉም፡፡ ኮሚሽነሩ ብዙም ስለስፖርቱ ፍላጎቱ (ኢንተረስቱ) ያላቸው አይመስልም፡፡ ለራሳቸውም ነግሬያቸዋለሁ፡፡  ይኼ ደግሞ በስፖርት አመራር ላይ ሊንፀባረቅ አይገባም፡፡ ከሚኒስትሯ ጋር በምክትልነት ሠርተዋል፡፡ ብዙም ስሜታቸውን አታየውም፡፡ አቶ መላኩ ጴጥሮስ እኮ የትናችሁ? ብለው ደውለው ኮተቤም ሆነ ሰበታ፣ እንጦጦም ይመጡ ነበር፡፡ አትሌቶቹን አነጋግረው በርቱ ብለው ይሔዳሉ፡፡ ጥሩ ነገር ካልመሰላቸው ከቢሮ ጠርተው ያወያያሉ፡፡ አሁን ምን ሠራህ? ምን ሠራሽ? የት ነው ያላችሁት ብሎ የሚባል ነገር የለም፡፡ አቶ መላኩን በጣም አጥተናቸዋል፡፡ ውጤታችንም እያዘቀዘቀ የመጣው ከዚያ በኋላ ነው፡፡ ግላዊ ጉዳይ አይደለም፡፡ ትክክለኛ ባለሙያ እርሳቸው ነበሩ፡፡

ሪፖርተር፡- እስካሁን በአትሌቲክሱ ለተገኘው ውጤት ክለቦች አስተዋጽዖ ነበራቸው፡፡ እንደማረሚያ፣ ኦሜድላ፣ መከላከያ አሁን ያለው አካሔድ ምን ይመስላል?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- ለክለቦች አክብሮትም፣ ዕውቅናም ብዙም የለም፡፡ አሠልጣኙ ሲናገር እርሱን መቅጣት፣ ማስጠንቀቅ፣ ማግለል እነዚህ ነገሮች አሉ፡፡ አትሌቱ መጀመርያ ከእናትና አባቱ፣ ከትምህርት ቤት በኋላ የምታገኘው ክለብ ውስጥ ነው፡፡ ክለብን አልፈው ወደ ብሔራዊ ሲመጡ ደግሞ አሠልጣኞቹን ያገሏቸዋል፡፡ ክለብ ቤታችን ነው፡፡ የአትሌቲክስ ልጁ ክለብ ነው፡፡ የክለብ አመራርና አደረጃጀት ወሳኝ ነው፡፡ ድጎማ ካስፈለገው ድጎማ ማድረግ ነው፡፡ ለክልሎች ብቻ ሳይሆን ለማረሚያ፣ ለሙገር፣ ለመከላከያ፣ ለፌዴራል ፖሊስ፣ ለባንክ፣ ወዘተ ክለቦች በዋነኛነት ድጎማም ዕውቅናም ሊሰጣቸው ይገባል፡፡ እነርሱን አግልሎ ልጆቹን የኔ ናቸው ሊባል አይገባም፡፡ የት ያውቃቸዋል? አልወለዳቸው፣ አላሳደጋቸው፣ ደሞዝ በኋላም ጡረታ የሚሰጣቸው ክለባቸው ነው፡፡ መጀመርያ ለክለቦች ዕውቅና ያስፈልጋል፡፡ ልጆቹን ብቻ ማለትም መሠረትን፣ ደራርቱን ብቻ ሳይሆን ክለባቸውን ባንክን፣ ማረሚያን፣ ፌዴራል ፖሊስን ማክበር አለብን፡፡ የክለቦቹ አደረጃጀት የፌዴሬሽኑ አደረጃጀት ሊሆን ይችላል፡፡ እርሱ ፊት ፊት እየሔደ ምሳሌ መሆን አለበት፡፡ አሠልጣኞችን መጥላት የለብህም፡፡ በእነርሱ የሠለጠኑና ከእነርሱ የወጡ ናቸው፡፡ በየክልሉ እየዞሩ እየመለመሉ አምጥተዋል፡፡ የልጆቻቸው ባለቤት ናቸውና አክብሮት ይገባቸዋል፡፡ ይኼ የለም፡፡ እንዲያውም አባርርሃለሁ የሚል ነገር ነው ያለው፡፡

ሪፖርተር፡- ኬንያውያን ብዛትም ጥራትንም አምጥተዋል፡፡ ታይቷል እኛ እምን ላይ ነን?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- እኛ ብዙ ጊዜ ጥራት ላይ እናተኩራለን፡፡ ምክንያቱም ሁሉን ለመርዳት ፌዴሬሽኑ አቅም የለውም፡፡ በጥራት ሆኖ ውጤታችንም የተሳካ ነው፡፡ አሁን ጥራቱም ብዙኀኑም (ማሱም) የለም፡፡

ሁለተኛ ክለብ ውስጥ ቢሆኑም ልምምዳቸው ከእኛ ጋር ነው፡፡ ከፌዴሬሽኑ ጋር ይሠራሉ፡፡ በኢትዮጵያ ሻምፒዮናና በአገር አቋራጭ ክለባቸውን ይወክላሉ፡፡ አንድ አራት ውድድሮች ለክለባቸው እንዲሮጡ ግዴታ ነው፡፡ ያን ካልሮጡ ለእኛም አይሮጡም፡፡ በመመርያው መሠረት ተስማምተን እንሠራ የነበረ ቢሆንም አሁን ግን ለክለባቸውም፣ ለአገርም አይሮጡም፡፡ ኃይሌ ለመጨረሻ ጊዜ የተወዳደረው በቤንጂንግ ኦሊምፒክ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ለክለቡም፣ ለአገሩም አልተወዳደረም፡፡ ቀነኒሳም ለዓለም ሻምፒዮና ብቻ ተወዳደረ እንጂ ለክለቡም አልተወዳደረም፤ ክለቡም አያውቀውም፡፡ በኋላ ልጆቹ ሩጫቸውን ሲያቆሙ ይጎዳቸዋል፡፡ ሮጠው ማዕርግ ያገኛሉ፡፡ ኮሌኔልነት የደረሱ አሉ፡፡ ግን ለየክለቦቻቸው ሮጠዋል ወይ? አካሔዱ ትንሽ ለቀቅ አድርጓል፡፡ ክለቦቻቸውን እንዲወዱ አላደረግንም፡፡

ሪፖርተር፡- አንዱ ነገር ለአዳዲስ አትሌቶች ትኩረት ያለመስጠት፣ ያለማሰለፍ ነገር ይታያል፡፡

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- ተስፋ ባላቸው ልጆች ላይ ትኩረት እናደርጋለን፡፡ በእኛም ላይ ያለው ተፅዕኖ አንዳንድ ጊዜ ያ ቋሚ የሆነውና ውጤት ያመጣው ልጅ ካለ ያኛውን ልጅ በርሱ ፋንታ ለመተካት አንሞክርም፡፡ ውጤት እስከሚያመጣ ድረስ፡፡ ቀነኒሳን በኃይሌ ለመተካት ብዙ ጭቅጭቅ ነበር፡፡ ፐርሰናልም ይመጣብሃል፡፡ ኃይሌ እኔ 10 ሺሕ ልሩጥ፣ እርሱ 5 ሺሕ ይሩጥ ያለበት ሁኔታ አለ፡፡ እርሱ ከፈለገ እኔ አልከለክለውም፤ በሁለቱም መወዳደር ይችላል፡፡ ቀነኒሳ በ10 ሺሕ አሸነፈ፤ በ5 ሺሕ ማጣርያውንም አለፈ፡፡ እኔ እንዲያውም ትደክማለህ ብዬው ነበር፡፡ ግዴለም ጋሼ ብቁ ነኝ ተማመነኝ ብሎ አሸነፈ፡፡ ጥሩነሽም እንደዚያው አደረገች፡፡

ሪፖርተር፡- የአትሌቲክስ ቡድኑ ከዴጉ መልስ ዋናው አሠልጣኝ በቂ ውጤት አግኝተናል ሲሉ፣ አትሌቶች ደግሞ ለኢትዮጵያ የማይገባ ውጤት ነው ብለዋል፡፡ የሁለቱም አነጋገር ተለያይቷል፡፡ በውጤቱ ደረጃ ዴጉ ኢትዮጵያን ይገልጻታል?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- የነበረን ውጤት ከላይ ነው፤ አሁን ግን ታች ሆነ፡፡ ራሱ ሁኔታውን ያስቀመጥልሃል፡፡ መከራከርም አያስፈልግም፡፡ በዚህ ዓመት ውጤት አለን፣ የለንም ውጤቱ ራሱ ምስክር ነው፡፡ ካለው፣ ሕዝብን ካስለመድነው አኳያ ያየነው አንድ ወርቅና አራት ነሐስ ብቻ ነው፡፡ ባለፈው ስንት ወርቅ፣ ብርና ነሐስ አግኝተናል? ሲነፃፀር ያሳየናል፡፡

ሪፖርተር፡- የለንደን ኦሊምፒክ ዓመት የማይሞላ ጊዜ ቀርቶታል፡፡ በዚህ አካሔዳችን ምን ማድረግ አለብን?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- ከዘጠኝ ወር ስንቱ የሥራ፣ ስንቱ የልምምድ ቀን ነው?  ያለው በጣም ያነሰ ጊዜ ነው፡፡ እኔ የምለው ሕዝቡና መንግሥት ተረባርበው አንድ አቋም ካልወሰዱ በስተቀር እንኳን ወርቅ ለማግኘት ነሐስም ያሰጋኛል፡፡ ስለዚህ ካሁኑ አስበንና ተወያይተን አንድ አቋም ተይዞ ሥራ ላይ ካልዋለ፣ ያ የለመድነው ‹‹ጉሮ ወሸባዬ›› በሐዘን ይለወጣል ብዬ ነው የማስበው፡፡ ከሙያ አኳያ ነው የምናገረው፤ ምኞታዊ ሆኜም አይደለም፤ ወይም ደግሞ ብቀላም አይደለም፡፡ አሠራራችን ለምንም አይበጀንም፤ ከምንም አያደርሰንም፡፡ እናም ይኸን ዘጠኝ ወር ወዲያም ወዲህ ብለን የምንሟሟተው ያሉትን ልጆች ይዘን ነው፡፡ ብዙዎቹም የዕድሜ ባለፀጋም፣ ውጤት ፈላጊዎችም እየሆኑ ነው፡፡ ውጤቱም የለም፡፡ እናም ውጤቱ ሚኒማ ብቻ ማምጣት አይደለም፡፡ ጥያቄው ብቃት ኖሯቸው ተወዳዳሪ ይሆናሉ ወይ ነው፡፡ እርሱ በጣም አስጊ ነው፡፡ አሁኑም ቢሆን አዲስም ቢሆን ሽማግሌም ቢሆኑ ጫናውን ችለው ውጤት የሚያመጣውንና የምታመጣውን ካሁኑ ካልወሰንን ብዙ ኪሳራ ውስጥ እንወድቃለን፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ የባሰ ያኮርፈናል፡፡ ስፖርቱንም ይጠላዋል፡፡ ስለዚህ መንግሥትም ይግባበት፤ ኮሚሽኑም ጣልቃ ገብቶ ማየት አለበት፡፡

ሪፖርተር፡- በለንደን ኦሊምፒክ የሚወዳደሩት በዴጉ የተሳተፉት ናቸው? ወይስ ሌላ ተተኪ አለን?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- የት አለ? እነኚህን ማነፅ ነው፡፡ ማን አለ? እነ ኃይሌ ቢሆኑም በማራቶን አስተማማኝ አይደሉም፡፡ በማራቶን በብዛት ልጆች አሉ ይባላል፡፡ ከነዚያ ውስጥ መራርጠህ በሦስትና አራት ወር ውስጥ ሚኒማውን የሚያሟሉ ከሆነ እነርሱን በየዕለቱ ተገቢውን ሥልጠና እየሰጡ ማድረስ ነው እንጂ አዲስ የምታመጣው ብዙ የለም፡፡ አሉ የሚባሉትን ከየክለቡ አምጥተህ በእነርሱ ላይ ጊዜ ብታጠፋ ጥሩ ይሆናል፡፡ አዲስ ግን ለወዲያኛው ኦሊምፒክ እንጂ ለለንደኑ የምትተምነው አይደለም፡፡

ሪፖርተር፡- በዓለም ሻምፒዮና ውጤታችን ላይ የኩባንያ ውድድሮች አሉታዊ ተፅዕኖ አሳድረዋል የሚባል ነገር አለ፡፡ በለንደኑስ አያሳስብም?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- የተጫወቱብንኮ ኩባንያዎቹ (ካምፓኒዎቹ) ናቸው፡፡ በአገሩ ምንም የማይሠራው በገንዘብ እያገናኘ እነርሱን እየሸጠ ነው የሚኖረው፡፡ ለእኛ አገር ምንም አልጠቀሙንም፡፡ ለልጆቹ ፍራንክ ትንሽ ትንሽ ይሰጣቸዋል፤ ለኢትዮጵያ ስፖርት ዕድገት ግን የሚያደርጉልን የለም፡፡ ከማጥፋት በስተቀር መፍትሔ የለም፡፡ ትልቁ ችግራችን እርሱ ነው፡፡ የኛም ሰዎች ከላይ እስከታች ማናጀር ውስጥ ገቡ፡፡ ግንኙነታቸው ከእነርሱ ጋር ነው፡፡ እኛንኮ አያነጋግሩንም ይፈሩናል፡፡  እኛ ውድድር ስናደርግ የማይመጣ ማናጀር የለም፡፡ ደላላ አይደለህም? ደላልነትህ ውጭ ነው እኛ ዘንድ አይደለም፤ አንፈልግም እንለዋለን፡፡ የደላሎች ነገር የባርያ ፍንገላ ዓይነት ነው፡፡ ኬንያውያን በጣም ቆራጥ ሆኑና አስወጥተው እንደገና ሀ ብለው ጀመሩ፡፡ አንድም ደላላ ዝር አይልም፡፡ አትሌቶቹ ያላቸው ስምምነት በዓለም አቀፍ ውድድር ላይ ያላቸው ኅብረት፣ ሲጫወቱ፣ ሲዘፍኑ ስታይ ልዩ ነው፡፡ አንዱ አሠልጣኝ ‹‹እኛ የእናንተን ወሰድን እናንተ ደግሞ የኛን ወሰዳችሁ›› ብሏል፡፡

ሪፖርተር፡- በአጭር ርቀት ሩጫ ያለን አካሔድ ምን ይመስላል?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- ከንጉሤ ሮባ ጀምሮ እንወዳደራለን፡፡ በሜልቦርን ኦሊምፒክ በ1949 ዓ.ም. ማሞ ወልዴ፣ ኃይሉ አበበ፣ በየነ አያኖ ተወዳድረዋል፡፡ ከሮም ኦሊምፒክ በኋላ ወደመካከለኛና ረዥም ርቀት አደላን እንጂ አጭር ርቀት ነበረን፡፡ ችግራችን ባጠቃላይ መሣርያም፣ ታርታን ትራክ (መም) የለንም፡፡ ክለቦቻችንም ሜዳም፣ ጅምናዚየምም የላቸውም፡፡ አጭር ርቀቱን የሚደጉም ምግብም የለንም፡፡ የምግብ ወጪ ያስፈልጋል፡፡ አዲሱ የውጭ አሠልጣኝ ጥያቄውም ይኸው ነው፡፡ ፕሮቲን ያስፈልጋል፡፡ ለረዥም ርቀት  የሚያስፈልገው ካርቦሃይድሬት ነው፡፡ ታዲያ የትኛውን፣ ስንቱንስ ታበላለህ? ክለብ ይኸን ያህል አያወጣልህም፤ ትልቁ ችግራችን ምግብና የማዘወተሪያ ስፍራው ነው፡፡ ክብደት ማንሣት አለብህ፤ ትልቅ ጅምናዚየም ያስፈልጋል፡፡ ጅምናዚየሙ ቢኖረንም አልተጠቀምንበትም፡፡  ወደ ረዥም ርቀቱ እየሸሸን ያለ ነው ለዚህ ነው፡፡

ሁለተኛ የአዲስ አበባ ስታዲየም መሮጫ ለውድድር ጥሩ ቢሆንም ለልምምድ ግን አይሆንም፡፡ ይጎዳሃል፡፡ ብዙዎች በሽተኛ ናቸው፡፡ እነ ኃይሌ እዚያ ልምምድ አይሠሩም፡፡ ድግግሞሽ ከሆነ ጫና ያበዛል፡፡ ለውድድር ግን ጥሩ ነው፡፡ እሱም እየተበላ ነው፡፡

ሪፖርተር፡- ተተኪ ማግኘት ይቻላል?

ዶ/ር ወልደ መስቀል
፡- ሰው አላጣንም፣ ሰው ሞልቷል፡፡ ሁሉ ነገር ከተሟላ በሦስትና አራት ዓመት ጊዜ ውስጥ ለኦሊምፒክ እናደርሳለን፡፡ ይኼ የለመድነው እንደ ባህልም ያደረግነው  ረዥም ሩጫ ምንጊዜም ልናጣው አይገባንም፡፡ እንደ ባህልም እንደ ሙያም ጭምር ነው፡፡ ማራቶን ለማሠልጠን ችግር የለብህም ምግብ ካለህ፡፡ ችግራችን የትራክ ጉዳይ ነው፤ አገር አቋራጭ ገንዘብ ስላለው ከትራክ ወደ ጎዳና ይወጣል፡፡ በአስፋልት ከተሮጠ ደግሞ ለአጭር ርቀት አይሆንም፡፡ ጭንህ ይበላሻል፤ ይኮማተራል፣ ይቋጠራል፡፡ ፊዚዮሎጂካሊም ማየት ያስፈልጋል፡፡ መሮጥ ብቻ አይደለም፡፡ ሥራው በደንብ ቢከናወን ማጣጣት እንችል ነበር፡፡ ልጆቹ በደንብ ሠርተው በአንድ መስመር ከሔዱ የነበረው ውጤታችን ይቀጥላል እንጂ አይቀንስም፡፡ አሁንኮ 5 ሺሕና 10 ሺሕ የለም፡፡ 12 ኪ.ሜ፣ ማራቶን ግባ ይሉታል፡፡ ልጆቹ በሙሉ በገንዘብ ምክንያት ተበላሹ፡፡ ይህን ያመጣው ድህነታችን ነው፤ ፈንድ ቢኖር ሊስተካከል ይችላል፡፡ የእኛ አገር ሀብታሞች እዚህ ላይ ኢንቨስት ማድረግ አይፈልጉም፡፡ ከዚያ ስም ሊያገኙ ይችላሉ፡፡ ግን አይፈልጉም፡፡ 

ሪፖርተር፡- የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በአዲስ አበባ በተዘጋጀበት ጊዜ ትልቅ መነሣሣት ታይቶ ነበር፡፡

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- በጣም እንጂ፡፡ እንደገና አደበዘዙት፡፡ ሰው ያያሉ፡፡ እኔ ብሸለም እኮ እኔ አይደለም የተሸለምኩት አገር ነው የተሸለመው፡፡ አንተ ስለተሸለምክ ሁሉም ያኮርፍሃል፡፡ እኔ ታዲያ ምን ላድርግ? መንግሥት ይገባሃል ብሎ ከሰጠኝ አመሰግናለሁ ብሎ መቀበል ነው፡፡ ሁሉም እንደየድርሻው አግኝቷል፡፡ እኔ ለሙያ፣ ለአገር ስል የሠራሁት እንጂ ገንዘብ አገኛለሁ ብዬ አይደለም፡፡ ደሞዝ አለኝ በእርሱ እኖራለሁ፡፡

ሪፖርተር፡- በሲዲኒና በቤጂንግ ኦሊምፒክ ከነበራችሁት አሠልጣኞች አሁን በዓለም ሻምፒዮና ምን ያህሉ አሉ?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- ማን አለ? ቤጂንግ ቶሎሳ፣ ሁሴን፣ ካሱ፣ ትእዛዙ ነበሩ፡፡ ከኦሊምፒክ በኋላ  የሚጠቀሙት በክለባቸው ነው፡፡ እኔን በመስከረም አስወጡኝ፡፡ ምንም አላሉ፤ ዝም ዝም አሉ፡፡ ከስድስት ወር በኋላ የራሴን ማሠልጠን ጀመርሁ፡፡ በአሁኑ ቡድን ቶሎሳም፣ ካሱም የሉበትም፡፡ ትእዛዙም ከኢትዮጵያ ወጥቷል፡፡ ሁሴን ግን አለበት፡፡

የረዥም ርቀት 5 ሺሕና 10 ሺሕ ዋናው አሠልጣኝ ይልማ በርታ ፔዳጎጂስት ነው፡፡ የምናገረው ግልጹን ነው፡፡ አሠልጣኝ ነኝ የሚለውን ወረቀት አምጣ ብለነው ነበር፡፡ የፊዚካል ኤዱኬሽን ዶክትሬት ይላል፡፡ ለዶክትሬት ሲታጩ እዚህ መጡ፤ ዶክተር ነን አሉ፡፡ ትምህርት ሚኒስቴር የለም ዕጩ ናችሁ አለ፡፡ ባለፈው ጊዜ መረጃውን አምጣ ተብሎ ሳያመጣ ቀረ፡፡ እኔ የሙያ ጉዳይ ስለሆነ አነሣዋለሁ፤ ግልጽ ነው  ተፃራሪነትም (አንታጎኒዝም) አይደለም፡፡ ማንም ቢሆን ቻሌንጅ ቢያደርገኝ ደስ ይለኛል፡፡ ሙያ ነው ቦታው ዝም ብሎ በይሆናል የሚባል ነገር አይሆንም፡፡ ንጉሤ ሮባ በትክክል የአትሌቲክስ አሠልጣኝ ነበር፡፡ ዲግሪ ነበረው፤ አስተማሪ መሆን ግን አይችልም፡፡ ‹‹ወልዴ ረዥም ርቀቱን ያዝ፣ እኔ ይሄን ልያዝ›› ብሎ ተስማምተን እንሠራ ነበር፡፡ ችግር ካለብህ ይነግርሃል፡፡ በጋራ እንሠራ ነበር፡፡ አይቶ ይኼ ልጅ ለዚህ ይሆናል ይልሃል፡፡ አበበ መኰንን ለውጤት ያበቃው እርሱ ነው፤ ተግባቢም ነው፡፡ እኔ ከሕዝብ በታች እንጂ በላይ አይደለሁም፡፡ ሙያ ቢኖረኝ በሙያዬ ማስመስከር አለብኝ እንጂ በግድ ይህን እመኑኝ ተቀበሉኝ ማለት አያስኬድም፡፡ የተማርኩትኮ ሕዝብን ለማገልገል ነው፡፡ ለመመጻደቅ አይደለም፡፡

ሪፖርተር፡- የውጭ ጥሪ መጥቶሎታል ይባላል?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- ውጭ አገር እንድሔድ ተጋብዣለሁ፡፡ ግን የአገሬ ስፖርት ሲሞት/ሲወድቅ ምን ማለት ነው? መሸሽ ነው? የት ለማን ነው ትቼ የምሔደው? በግሌም ቢሆን ይኸው አንድ ዓመቴ  በጃንሜዳ እየሠራሁ ነው፡፡ ለምን እሸሻለሁ? አሜሪካ ሔጄ ብዙ ጥሪዎች ነበሩኝ ምን ያደርግልኛል? አልፈልግም፡፡ ለሆዴ ከሆነ ከጡረታዬ ጋር መንግሥትም ሕዝብም ያበላኛል፡፡

ሪፖርተር፡- አሁን ምን እየሠሩ ነው?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- እያረፍኩ ነው፡፡ የጡረታ ብር ብዙ ነው፤ እርሱን እየበላሁ መቀመጥ ነው፡፡

ሪፖርተር፡-  ስንት ይከፈልዎታል?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- ወደ 765 ብር፡፡ እኔ ወደዚህ ስዞር አቶ መላኩ የምንሰጣችሁ ገንዘብ በጣም ትንሽ ስለሆነች በኮንትራት ላስቀጥርህ አለኝ፤ ከ1500 ብር 7000 ተሰጠኝ፡፡ ተቆራርጦ ወደ 5000 ብር ይደርሳል፡፡ ይኼን እያገኘሁ ለምን ፈረንጅ አገር እሔዳለሁ አልኩ፡፡ የጡረታ አበል በኢሕአዴግ ጊዜ ተሻሻለ የእኛ እዚያው ላይ ተወስኗል፡፡

ሪፖርተር፡- በዴጉ ሻምፒዮና በተገኘው ውጤት በግልዎ  የተሰማዎት ምንድን ነው?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- ቤቴን ዘግቼ ነው ያለቀስኩት፡፡ ምክንያቱም ያሁኑ ውጤት አይደለም፡፡ አለመዘጋጀታችን ይሰማኝ ነበር፡፡ ግን ለዚያ ውድድር ምንጊዜም ብቃት ያላቸውን ልጆች እናዘጋጃለን፡፡

ሪፖርተር፡- ምን መልእክት ያስተላልፋሉ?

ዶ/ር ወልደመስቀል
፡- ለስፖርታችን ደህና ጊዜ ይምጣለት ነው፡፡ በጋራ ለአገራችን፣ ለሰንደቅ ዓላማችን፣ ለብሔራዊ መዝሙራችን ተዘጋጅተን እንሥራ፡፡ በጋራ እንጣር፡፡ ሀቀኝነት ይኑር፤ ወገናዊነት፣ አድሏዊነት፣ ጠባብነት ይቅር፡፡ የስፖርት መርሑ ይኼ ነው፡፡ ስፖርት በጎሳ፣ በሃይማኖት፣ በቀለም አይከፈልም፡፡ ይኼንን መርሕ አድርገን በዚህ ከሠራን ምናልባት የሸሸን ውጤት ይመጣል ብዬ አምናለሁ፤ ምኞቴም ነው፡፡

No comments:

Post a Comment