Sunday, December 8, 2013

ከሳዑዲ ለሚመለሱ ኢትዮጵያውያን 13.1 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ተጠየቀ

Ethiopian Reporter
ዓለም አቀፍ የስደት ድርጅት (አይኦኤም) ከሳዑዲ ዓረቢያ ለተመለሱና...

ቁጥራቸውም 120 ሺሕ እንደሚደርስ ለሚገመቱ ተመላሽ ኢትዮጵያውያን 13.1 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ እንዲደረግ ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ጥያቄ አቀረበ፡፡ ድርጅቱ እንደሚለው ከስደት ተመላሾቹ ቁጥር በፍጥነት እየጨመረ በመሆኑ የ24 ሰዓት አጣዳፊ ዕርዳታ ያስፈልጋል፡፡ እስካለፈው ሐሙስ ኅዳር 26 ቀን 2006 ዓ.ም. ድረስ የኢትዮጵያ መንግሥት ከ100 ሺሕ በላይ ተመላሾችን መቀበሉን ያስታወቀው አይኦኤም፣ ከእነዚህ ውስጥ ከ90 ሺሕ በላይ ለሚሆኑ የስደት ተመላሾች የቀጥታ ድጋፍ ማድረጉን አስታውቋል፡፡ በየቀኑም ከሰባት ሺሕ በላይ ስደተኞች እየተመለሱ ናቸው ብሏል፡፡ አይኦኤም ለትራንስፖርት፣ ለሕክምና፣ ለምግብና ለተዛማጅ አገልግሎቶች ድጋፍ እያደረገ መሆኑን አስታውቆ፣ ቤተሰብ ለሌላቸው 167 ልጆች ዕርዳታ ማድረጉን ገልጿል፡፡


ሃምሳ ስምንት ሕፃናትን ከመንግሥት ጋር በመተባበር ወደ ቤተሰቦቻቸው መሸኘቱን አስታውቋል፡፡ አይኦኤም 2.5 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ቢያገኝም፣ የ13.1 ሚሊዮን ዶላር ክፍተት ስላለ፣ የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ድጋፍ እንደሚያስፈልገው አስታውቋል፡፡ ለእያንዳንዱ ተመላሽ በነፍስ ወከፍ 130 ዶላር እንደሚያስፈልገው ገልጿል፡፡ እስካሁን ዩኒሴፍ፣ ዩኤንኤችሲአር፣ የዓለም ምግብ ፕሮግራም፣ የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር፣ የዓለም ቀይ መስቀል ኮሚቴና ሌሎች አካላት የተለያዩ ድጋፎችን ማድረጋቸውን አስታውቋል፡፡
http://www.ethiopianreporter.com

No comments:

Post a Comment