Monday, December 23, 2013

ቴዲ ከበደሌ ጋር ለ1 ዓመት ኮንሰርት ሊሰራ ነው

ኮንሰርቱ በጥር ወር በድሬዳዋ ይጀመራል
ታዋቂው ድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) “የፍቅር ጉዞ” የተሰኘ  ለአንድ አመት የሚዘልቅ የሙዚቃ ኮንሰርት ለመስራት ከበደሌ ስፔሻል ጋር ሰሞኑን የተፈራረመ ሲሆን ኮንሰርቱ ጥር ሶስት ቀን በድሬዳዋ እንደሚጀመር ተገለፀ፡፡
ቴዲ አፍሮ፣ ማናጀሩ፣ እንዲሁም የሄኒከንና የበደሌ ቢራ ስራ አስኪያጆች ትላንት በሂልተን ሆቴል በጋራ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤ የኮንሰርቱ የአንድ አመት ቆይታ ከቴዲ አፍሮ ጋር ታሪካዊና የተሳካ ይሆናል ብለዋል፡፡ “በደሌ ስፔሻል ቀደም ሲል ብሄራዊ የእግር ኳስ ቡድኑን (ዋልያን) ስፖንሰር በማድረግ ታሪክ ሰርቷል” ያለው ቴዲ አፍሮ፤ “እኔም ከበደሌ ስፔሻል ጋር የማደርገው የአንድ አመት የሙዚቃ ድግስ ጉዞ ታሪካዊ እንደሚሆን አልጠራጠርም” ብሏል፡፡

“የፍቅር ጉዞ” የሙዚቃ ድግስ ዋና አላማው፤ ኢትዮጵያዊያንን በፍቅር አንድ ማድረግ እንደሆነ የገለፀው ቴዲ አፍሮ፤ “ምንም እንኳን የተለያየ ቋንቋና ባህል ቢኖረንም አንድ አገር ውስጥ እንደመኖራችን የአለም ቋንቋ በሆነው ሙዚቃ ህብር ፈጥረን አንድ እንሆናለን” ብሏል፡፡ አርቲስቱ ከአቦጊዳ ባንድ ጋር የሚያቀርበው ኮንሰርት፤ በድሬዳዋ፣ ጂማ፣ አዳማ፣ አዲስ አበባ እና በሌሎች የአገሪቱ ከተሞች ይካሄዳል ተብሏል፡፡ “ጥቁር ሰው” የተሰኘ አልበሙ ሲወጣ ስፖንሰሩ ሜታ ቢራ እንደነበር ያስታወሰው የቴዲ አፍሮ ማናጀር አቶ ዘካሪያስ ጌታቸው፤ ከሜታ ጋር በሰላምና በፍቅር ስራቸውን ጨርሰው ወደ በደሌ ስፔሻል መምጣታቸውን ገልጿል፡፡ በደሌ ስፔሻል ለአንድ አመቱ የሙዚቃ ድግስ ጉዞ ምን ያህል በጀት እንደመደበ ከአዲስ አድማስ ለቀረበው ጥያቄ የበደሌ ስፔሻል ስራ አስኪያጆች፤ “ጉዳዩ ምስጢር ነው፤ ይፋ አናደርግም” በማለት ምላሽ ከመስጠት ተቆጥበዋል፡፡ የሄኒከን ማናጀር ሚስተር ዮሀንዱዌርስ ኮንሰርቱን አስመልክተው ባደረጉት ንግግር፤ በደሌ ስፔሻል፤ ታዋቂና ተወዳጅ ከሆነው ድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሣ ጋር የአንድ አመት የፍቅር ጉዞ ለማድረግ ኩባንያቸው መወሰኑ እንዳስደሰታቸው ገልፀው፣ የቴዲና የበደሌ የአንድ ዓመት ቆይታ አይረሴ ይሆናል ብለው እንደሚያምኑ ገልፀዋል፡፡ ኮንሰርቱ በድሬዳዋ ከተጀመረ በኋላ ጅማ፣ አዳማ፣ አዲስ አበባና ሌሎች ክልሎችን ያዳርሳል ተብሏል፡፡
http://addisadmassnews.com

No comments:

Post a Comment