Wednesday, June 5, 2013

አቶ በከር ሻሌ በሚኒስትር ማዕረግ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሆነው ተሾሙ


•    በዓመቱ ውስጥ ሲሾሙ ለሦስተኛ ጊዜ ነው

በከፍተኛ የሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ሥር በዋሉት በሚኒስትር ማዕረግ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ መላኩ ፈንታ ምትክ፣ የአዳማ ከተማ ከንቲባ አቶ በከር ሻሌ ተሾሙ፡፡
በሚኒስትር ማዕረግ የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሆነው እንዲሠሩ ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ የሹሙት ደብዳቤ የደረሳቸው አቶ በከር፣ ለባለሥልጣኑ አዲስ አይደሉም፡፡



አቶ በከር በዚሁ ዓመት ለሦስተኛ ጊዜ ሹመት ማግኘታቸው የታወቀ ሲሆን፣ በሚኒስትር ዴኤታነት የገቢዎችና ጉምሩክ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሆነው ለወራት ሠርተዋል፡፡

ከገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተርነት ተነስተው ወደ ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ተዛውረው የነበሩት አቶ በከር፣ በጽሕፈት ቤቱ ለተወሰኑ ወራት በሚኒስትር ዴኤታነት ካገለገሉ በኋላ በቅርቡ የአዳማ ከተማ ከንቲባ ሆነው መሾማቸው የሚታወስ ነው፡፡

የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሆነው መሾማቸው ለሠራተኞች ይፋ የተደረገው፣ ሠራተኞች የግንቦት 20 በዓልን በባለሥልጣኑ ዋና መሥርያ ቤት ቅጥር ግቢ ባከበሩበት ቀን ቢሆንም፣ በሹመት ደብዳቤያቸው ላይ የተጠቀሰው የሥራ መጀመሪያቸው ቀን ከግንቦት 21 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ እንደሚል የሪፖርተር ምንጮች ገልጸዋል፡፡

ከከፍተኛ የሙስና ወንጀል ጋር በተያያዘ ዋናና ምክትል ዳይሬክተሩን ጨምሮ የናዝሬትና የሚሌ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች ሥራ አስኪያጆች፣ ሠራተኞች ተጠርጥረው በእስር ላይ በመሆናቸው፣ አቶ በከር ከፍተኛ የሥራ ጫና እንደሚገጥማቸው ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው አስተያየት ሰጪዎች ያስረዳሉ፡፡

በኦሮሚያ ክልል በተለይ በአዳማ ከተማ ከንቲባዎች መቀያየራቸውን ተከትሎ፣ አቶ በከር አዳማን ለመጨረሻ ጊዜ ለማረጋጋት በሚል መሾማቸው የሚታወስ ነው፡፡ ወደ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን መመለሳቸው ሥራውን ከማወቃቸው በተጨማሪ ትክክለኛ ምርጫ እንደሆኑ እየተነገረ ነው፡፡



http://www.ethiopianreporter.com

 

No comments:

Post a Comment