Wednesday, November 21, 2012

የዘጠኝ ቀን ሕፃን ከየካቲት 12 ሆስፒታል ተሰረቀች

የካቲት 12 ሆስፒታል

በታምሩ ጽጌ

ጥቅምት 27 ቀን 2005 ዓ.ም. በየካቲት 12 ሆስፒታል የተወለደች ሕፃን፣ በተወለደች በዘጠነኛው ቀንዋ ኅዳር 5 ቀን 2005 ዓ.ም. መሰረቋን ወላጅ እናቷ ለሪፖርተር ገለጸች፡፡ የሕፃኗ እናት ወ/ሮ በላይነሽ አያሌው እንደገለጸችው፣ ልጇን የተገላገለችው የካቲት 12 ሆስፒታል ጥቅምት 27 ቀን 2005 ዓ.ም. በኦፕራሲዮን ነው፡፡ የሆስፒታሉ ሐኪሞች የኦፕራሲዮኑን ስፌት ለመፍታት በሳምንቱ ይቀጥሯታል፡፡ በወለደች በዘጠነኛ ቀንዋ ኅዳር 5 ቀን 2005 ዓ.ም. የበኩር ልጇን ይዛ ወደ ሆስፒታሉ መሄዷን ተናግራለች፡፡

ወ/ሮ በላይነሽ ወደ ሆስፒታሉ ያመራችው ከጓደኛዋ ጋር ቢሆንም፣ የመታከሚያ ካርዷን ረስታ በመሄዷ ጓደኛዋ እንድታመጣላት ወደ ቤት ትልካታለች፡፡ በጣም አሟት ስለነበር ልጇን ታቅፋ ለመቀመጥ አለመቻሏንና መንቆራጠጧን ያየች አንዲት ወጣት ተጠግታ “ልያዝልሽ” ብላ እንደጠየቀቻት የተናገረችው ወ/ሮ በላይነሽ፣ አሟት ስለነበር ያለምንም ማቅማማት ትሰጣትና አጠገቧ መቀመጧን ገልጻለች፡፡



ካርድ ልታመጣ የሄደችው ጓደኛዋ ቶሎ ብትመለስም፣ ሕፃኗን ሌላ ሰው አቅፏት በማየቷ በሆስፒታሉ ውስጥ ወልዳ የተኛች ሌላ ጓደኛዋን ልትጠይቅ ስትሄድ፣ ከካርድ ክፍል የመጣች ሠራተኛ “ካርድ ያላወጣ ታካሚ” ብላ ስትጣራ ወ/ሮ በላይነሽ ወደ ካርድ ክፍል ትሄዳለች፡፡

ጓደኛዋ ከሄደችበት ስትመለስ ወ/ሮ በላይነሽን በማጣቷ ሕፃኗን የታቀፈችውን ወጣት ትተውና ወደ ካርድ ክፍል በማምራት፣ እሷን እንድትመለስ አድርጋ ካርዱን እሷ ልታወጣ መሄዷን ወ/ሮ በላይነሽ አስረድታለች፡፡

ወ/ሮ በላይነሽ ተመልሳ ወደ መታከሚያው ክፍል ስትደርስ “ልያዝልሽ” ያለቻት ወጣት ልጇን ይዛ መሰወሯን ገልጻለች፡፡

በወቅቱ በመጮህ ልጇ መጥፋቷን በግቢው ብታውጅም፣ ሕፃኗን ይዛ የተሰወረችውን ወጣት ማግኘት አለመቻሏንና ያላት ዕድል ለፖሊስ ማሳወቅ በመሆኑ፣ ለፖሊስ አስመዝግባ እስከዛሬዋ ቀን ድረስ የፖሊስን ምላሽ በመጠባበቅ ላይ መሆኗን ለሪፖርተር ተናግራለች፡፡

ሆስፒታሉ ረዳት የሌላቸውን ወላዶች ነርሶቹ ወይም የጤና ባለሙያዎቹ እንዲረዷቸው ለምን እንደማያደርግ፣ በሆስፒታሉ ውስጥ ስለጠፋችው ሕፃንና ሆስፒታሉ ስላለው የጥበቃ ሁኔታ ማብራሪያ እንዲሰጡ በየካቲት 12 ሆስፒታል በመገኘት  ለማነጋገር የተደረገው ጥረት፣ ሥራ አስኪያጁና ሜዲካል ዳይሬክተሩ ሙሉ ቀን ስብሰባ ላይ መሆናቸውን ከመግለጽ ውጭ፣ የሚመለከታቸው ዶክተሮችና የሥራ ሒደት ባለቤቶች “የበላዮቹ ካላዘዙበት አንናገርም” በማለታቸው አስተያየታቸውን ማካተት አልተቻለም፡፡

ሕፃናትን በመስረቅ ለተለያዩ የውጭና የአገር ውስጥ የሕፃናት ማሳደጊያ ድርጅቶች የሚሸጡ እንዳሉ በስፋት ይነገራል፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ ወደማይታወቅ ቦታ በመውሰድ አካላቸውን በማጉደል ለልመና እንደሚጠቀሙባቸውም ይነገራል፡፡ ኅብረተሰቡና መንግሥት ትኩረት ሰጥቶ በመከታተል በተለይ የሚያሳድጉና ለውጭ በማደጐነት የሚያስተላልፉ ድርጅቶች፣ ሕፃናቱን ከየትና በምን ሁኔታ እንዳገኟቸው መቆጣጠር እንደሚገባ የሚናገሩ ብዙዎች ናቸው፡፡ በልመና ላይ የተሰማሩ ዜጎችም ሕፃናቱን ከየት እንዳመጧቸው መጠየቅም ተገቢ መሆኑን ብዙዎች ያሳስባሉ፡፡
http://www.ethiopianreporter.com

No comments:

Post a Comment