Wednesday, May 9, 2012

ለንግሥ ወደ ደቡብ ወሎ የተጓዙ 17 ሰዎች በመኪና አደጋ ሕይወታቸው አለፈ


በአማራ ክልል በደቡብ ወሎ ዞን አማራ ሳይንት ወረዳ በምትገኘውና ዛሬ በምትነግሠው ርእሰ አድባራት ተድባበ ማርያም ገዳም ለንግሥ በመጓዝ ላይ የነበሩ 17 ሰዎች፣ በደረሰባቸው የመኪና መገልበጥ አደጋ ከትናንትና በስቲያ ሕይወታቸው ማለፉን በስፍራው የነበሩ የዓይን እማኞች ለሪፖርተር ገለጹ፡፡ ከትናንት በስቲያ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ሲሆን በደረሰው የመኪና መገልበጥ አደጋ 17 ሰዎች ወዲያውኑ ሕይወታቸው ማለፉን፣ ሁለት ሰዎች ወደ ደሴ ሆስፒታል መላካቸውን፣ ሁለት ደግሞ ሳይንት አጅባር ህዳር 11 ሆስፒታል መግባታቸውንና አንድ ተጐጂ ደግሞ ሳይንት አጅባር ጤና ጣቢያ ዕርዳታ እየተደረገላቸው እንደሚገኙ እማኞቹ ተናግረዋል፡፡

ሕይወታቸው ካለፉት 17 ሰዎች መካከል አሥሩ እዚያው ተድባበ ማርያም ገዳም የቀብር ሥርዓታቸው በትናንትናው ዕለት ከምሽቱ 11 ሰዓት መፈጸሙን፣ የቀሪዎቹ አስከሬን ወደ አዲስ አበባና ወደየመጡበት አካባቢ እየተሸኘ መሆኑንም አስታውቀዋል፡፡

ከአዲስ አበባ በ600 ኪሎ ሜትርና ከሳይንት አጅባር በ40 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኘው የተድባበ ማርያም ገዳም ለመድረስ ጥቂት ርቀት ሲቀር ባለው ገደላማ ቦታ ላይ ሲደርስ፣ አንድ መነኩሴና ሁለት ወጣቶች ወርደው በእግራቸው መጓዝ በመጀመራቸው ከአደጋው መትረፋቸውን እማኞቹ ገልጸዋል፡፡ በመኪና አደጋው ሕይወታቸው ላለፈውና የቀብር ሥርዓታቸው በዚያው በገዳሙ ለተፈጸመው ምዕመናን ብፁዕ አቡነ ገብርኤል በተገኙበት በፈረንሳይ አቦ ቤተ ክርስቲያን ትናንት ምሽት ላይ ፀሎተ ፍትሐት መደረጉን ምንጮች ገልጸዋል፡፡

No comments:

Post a Comment