Wednesday, September 12, 2012

የሥልጣን ሽግግሩ በጉጉት እየተጠበቀ ነው ፡፡ተጨማሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮች ሊሾሙ ይችላሉ፡፡


የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊን የቀብር ሥርዓት በብሔራዊ ደረጃ ፈጽሞ በዚህ ሳምንት ለሥልጣን ሽግግር ቀጠሮ የያዘው ኢሕአዴግ፣ የምክር ቤቱን ስብሰባ ሰሞኑን ያደርጋል፡፡ በአገሪቷ ታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ይደረጋል ተብሎ የሚጠበቀው ሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር በሕዝቡና በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ዘንድ ከፍተኛ ጉጉት ፈጥሯል፡፡

በሳምንቱ መገባደጃ ላይ የሚደረገው የኢሕአዴግ ምክር ቤት ስብሰባ የኢሕአዴግ ሊቀመንበርንና ምክትል ሊቀመንበር የሚመርጥ ሲሆን፣ የግንባሩ ሊቀመናብርት በመንግሥት መዋቅር ደግሞ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትርና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ይሆናሉ፡፡ በዚህ መሠረት አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ለቀጣዮቹ ሦስት ዓመታት የግንባሩ ሊቀመንበርና የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር እንደሚሆኑ እየተጠበቀ ነው፡፡ የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ማንነት ግን እስካሁን በይፋ አልታወቀም፡፡



በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 73 መሠረት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሲመረጥ፣ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አብላጫ መቀመጫ ያለው የፖለቲካ ድርጅት ወይም ያላቸው የፖለቲካ ድርጅቶች የመንግሥት ሥልጣን ይረከባል ወይም ይረከባሉ፡፡ በዚህ መሠረት በፓርላማው 99.6 በመቶ መቀመጫ ያለው ኢሕአዴግ ሲሆን፣ የኢሕአዴግን አመራር የሚረከቡት ግለሰቦች በዚህ ሒደት የመንግሥትን መዋቅር ለመምራት በፓርላማ ይሰየማሉ ማለት ነው፡፡

በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 74 ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ከተሰጡ ሥልጣናትና ተግባራት ውስጥ በጉልህነት የሚጠቀሰው በንዑስ አንቀጽ አንድ ላይ የሰፈረው ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአገሪቱ ርዕሰ መስተዳድር፣ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ሰብሳቢና የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ነው፡፡ በቀሪዎቹ አሥራ ሁለት አንቀጾች መሠረት አስፈጻሚ የሚባለውን የመንግሥት አካል በሙሉ ኃላፊነት ይመራል፡፡ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 75 መሠረት ደግሞ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ተለይተው የሚሰጡትን ተግባሮች ያከናውናል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማይኖርበት ጊዜ ተክቶት ይሠራል፡፡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ መሆኑ በሕገ መንግሥቱ ውስጥ ሰፍሯል፡፡

በሳምንቱ ማገባደጃ ላይ የሚሰበሰበው የኢሕአዴግ ምክር ቤት የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሊሆን የሚችለውን የግንባሩን መሪ ሲሰይም የግንባሩን ምክትል ሊቀመንበርም እንደሚመርጥ ይታወቃል፡፡ የግንባሩ ምክትል ሊቀመንበር ደግሞ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡ ይህ አሠራር ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ አገሪቱን በመሩባቸው 21 ዓመታት ታይቷል፡፡ የኢሕአዴግ ሊቀመንበር የነበሩት አቶ መለስ ፕሬዚዳንት በነበሩበት ወቅት የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ታምራት ላይኔ የግንባሩ ምክትል ሊቀመንበር ነበሩ፡፡ በእሳቸው እግር የተተኩት አቶ አዲሱ ለገሠ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የግብርና ሚኒስትር በነበሩበት ወቅት የግንባሩ ምክትል ሊቀመንበር ነበሩ፡፡ አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ሲሆኑ የግንባሩ ምክትል ሊቀመንበር ሆነዋል፡፡

እስካሁን ባለው የተረጋገጠ መረጃ መሠረት አቶ ኃይለ ማርያም የግንባሩ ሊቀመንበርና የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር እንደሚሆኑ ሲጠበቅ የምክትላቸው ማንነት ግን ሊታወቅ አልተቻለም፡፡ ይኼም ብቻ አይደለም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በሞት ከተለዩ በኋላ ሊፈጠር የሚችለውን ክፍተት በስፋትና በምልዓት ለመድፈን የኢሕአዴግ አመራር ርብርብ ለማድረግ መዘጋጀቱን በተደጋጋሚ ለሕዝብ ገልጿል፡፡ በዚህ መሠረት ለአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ከፍተኛ እገዛ ለማድረግ ሲባል ተጨማሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮች ሊሾሙ እንደሚችሉ ይሰማል፡፡ ዋነኛ የተባሉ ስትራቴጂካዊ ተቋማትን በተለያዩ ዘርፎች በመከፋፈልና የአዲሱና የነባሩ አመራር አባላት በመዋሀድ የተጀመሩ ሥራዎችን ለማስቀጠል እንደታሰበ ጭምጭምታዎች ይሰማሉ፡፡ ምንም እንኳ በሕገ መንግሥቱ ስለ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ቢወሳም የተለያዩ ዘርፎችን የሚመሩ ምክትሎችን መሾም ምንም ችግር እንደሌለው የሕግ ባለሙያዎች ይገልጻሉ፡፡ በሕገ መንግሥቱ እስካልተገለጸ ድረስ አንድም ብዙም መሾም ይቻላል በማለት ያስረዳሉ፡፡

አዲሱን የሥልጣን ሽግግር በተመለከተ በተለይም ደግሞ የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮች ሹመት ላይ አስተያየታቸውን የተጠየቁ ባለሙያዎች እንደሚሉት፣ ሁኔታዎችን በሁለት ፈርጆ ማየት ይገባል፡፡ የመጀመርያው የፓርቲ ወይም የብሔር ተዋጽኦን በተመለከተ ሲሆን፣ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮቹ የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶችን ውክልና ይዘው በተዋጽኦ የሚመረጡ ከሆነ ዓላማው የሥልጣን ክፍፍል ይሆናል በማለት ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የደቡብ ፓርቲን ሲወክሉ፣ የተቀሩት አዲስ የሚሾሙት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮች የአማራ፣ የትግራይና የኦሮሚያ አባል ፓርቲዎችን ይወክላሉ፡፡ በዚህ መሠረት የፓርቲ ፖለቲካው አይሎ የሥልጣን ድልድል ብቻ ይሆናል በማለት ይገልጻሉ፡፡ እንዲህ ዓይነቱ አካሄድ ከድርጅታዊ መደላደል ያላለፈ፣ ለውጥ ለማስመዝገብ ፋይዳ የሌለውና አጠያያቂ ነው በማለት ይገልጹታል፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ የሥልጣን ሽግግሩ እንደተባለው የተጀመሩ የልማት ውጥኖችን ከግብ ለማድረስ ከሆነ ደግሞ የብቃት ጉዳይ ወሳኝ በመሆኑ፣ አዲሱን ጠቅላይ ሚኒስትር በሥራ ማገዝ የሚችሉ ብቃት ያላቸው ተሿሚዎች ይመጣሉ፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ሕልፈት ተከትሎ ሊኖር የሚችለውን ክፍተት ለመሙላት የብቃት ጉዳይ በእጅጉ ሊታሰብበት ይገባል የሚሉት አስተያየት ሰጪዎች፣ እንዲህ ዓይነቱ አሿሿም በአዎንታዊ ጐኑ መታየት አለበት ይላሉ፡፡ የሥልጣን ሽግግሩ በብቃት ላይ ትኩረት ካደረገ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን በብቃት ለማስፈጸም በእጅጉ ጠቃሚ ነው ተብሏል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ አዲሱና የቀድሞው አመራር በጋራ ተቀናጅተው ይሠራሉ ተብሎ በኢሕአዴግ መነገሩ ምንን ያመለክታል የሚሉም እንዲሁ አሉ፡፡ በአዲሱ አሿሿም ላይ የድሮዎቹም አመራሮች ይኖራሉ ማለት ነው? በማለት ይጠይቁና፣ ቀደም ካለው ጊዜ ጀምሮ ሲቀነቀን የነበረውን የመተካካት ዕቅድ አያፋልሰውም ወይ የሚሉ ጥያቄዎችን ያነሳሉ፡፡ ለዚህ ምላሽ አለን የሚሉ ወገኖች ደግሞ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ሕልፈት ምክንያት ሊኖሩ የሚችሉ ክፍተቶች መደፈን ስላለባቸው አዲሱ አመራር የግድ የቀድሞውን አመራር ድጋፍ ይሻል ይላሉ፡፡ አቅም ያላቸው አመራሮች የግድ ካልተተኩ ተብሎ ወደ ጎን መግፋት አይገባም በማለት ጭምር፡፡

እስከሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት ድረስ የኢሕአዴግ አመራሮች ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊን ጨምሮ ተራ በተራ ይተካሉ ተብሎ እንደነበር የሚያስታውሱ ደግሞ፣ አሁን ባለው አካሄድ ነባሮቹን አለማካተት ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ ያመዝናል ባይ ናቸው፡፡ ቀሪዎቹ ሦስት ዓመታት የመተካካቱ ሒደት የሚከናወንባቸው በመሆናቸው አሁኑኑ አዲሱ አመራር ሙሉ በሙሉ ይተካ ማለት ይከብዳል ይላሉ፡፡ በተለይም የአምስት ዓመቱን የዕድገትና የትራንስፎርሜሸን ዕቅድና የህዳሴውን ግድብ ጨምሮ ግዙፍ የመሠረተ ልማቶችን ለማጠናቀቅ የአዲሱና የነባሩ አመራር ውህደት ከምንጊዜውም በላይ አስፈላጊ ነው በማለት ይከራከራሉ፡፡ ሌላው ቀርቶ በአምባሳደርነት የተሾሙ ልምድ ያላቸው የአመራር አባላት ሳይቀሩ ለዚህ ወሳኝ ጊዜ አገልግሎታቸው ቢፈለግ የተሻለ ይሆናል በማለት ሐሳብ ያቀርባሉ፡፡

ከአዲሱ አመራር አባላት በዕውቀታቸውና በሚያከናውኑት ተግባር አንቱ የተሰኙ ተስፋ ያላቸው አመራሮች በሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት ውስጥ በሚደረገው የመተካካት ሥራ የበለጠ አቅምና ተቀባይነት ስለሚያዳብሩ፣ የሁለቱን ወገን ስብጥር ለዚህ ጊዜ መጠቀም ብልህነት ነው በማለትም ይመክራሉ፡፡ በውጭ ጉዳይ ዘርፍ በተለይ በዲፕሎማሲው መስክ በአፍሪካ አኅጉርና በአፍሪካ ቀንድ አካባቢ የኢትዮጵያን ተደማጭነት ማጠናከርና ከጎረቤት አገሮች ጋር በሰላምና በትብብር መንፈስ መሥራት የሚሉትን ይጠቅሳሉ፡፡ መንግሥት እየመሠረተች ያለችውን ሶማሊያ በማገዝ በአካባቢው ፀጥታን ማስፈንና የሱዳንና የደቡብ ሱዳንን ውዝግብ መፍታት አለበት፡፡ ይህ ደግሞ ልምድና ጥበብ ይጠይቃል ይላሉ፡፡ አገሪቱ በአፍሪካ ኅብረት፣ በአውሮፓ ኅብረት፣ በአሜሪካና በሌሎች ዓለም አቀፍ ደረጃዎች በብቃት ለማሳተፍ የአዲሱና የነባሩ ውህደት የግድ ነው ይላሉ፡፡

የተጀመሩት ግዙፍ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች በነበሩበት ፍጥነት ከተቻለም በከፍተኛ ፍጥነት እንዲጓዙ ለማድረግ፣ ቀጥታ የውጭ ኢንቨስትመንት በአስተማማኝ ሁኔታ ለመሳብ፣ ማክሮ ኢኮኖሚውን ለማረጋጋት፣ ከአቅም በላይ የሆነውን የኑሮ ውድነት ለማርገብ፣ ተጨማሪ የሥራ ዕድሎችን ለመፍጠር፣ ብድሮችንና ዕርዳታዎችን በአስተማማኝ ለማግኘት፣ ወዘተ የርብርብ ሥራ ስለሚጠይቅ የአዲሱና የቀድሞው አመራር ውህደት አስፈላጊነትን አፅንኦት ይሰጣሉ፡፡

የኢሕአዴግ ምክር ቤት በዚህ ሳምንት የግንባሩን ዋናና ምክትል ሊቀመናብርት ማንነት ካሳወቀ በኋላ ቀሪው ሥራ የፓርላማው ይሆናል፡፡ በመስከረም ወር የመጨረሻው ሳምንት ላይ ሦስተኛ ዓመት የሥራ ዘመኑን የሚጀምረው ፓርላማ የሥልጣን ሽግግሩን ጠቅላይ ሚኒስትሩን በመምረጥ ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ‹‹መለስን መተካት ከባድ ነው›› ያሉት አባባል በኢሕአዴግ አመራር አባላትም ዘንድ ግንዛቤ የተያዘበትና እንዲሁም ድርጅቱ በጋራ አመራር የሚያምን በመሆኑ ይህንን ተግባራዊ እንደሚያደርገው ውስጥ አዋቂዎች ይናገራሉ፡፡

የመተካካቱ ሒደት ቢያልቅ እንኳን አብዛኞቹ የአመራር አባላት ድርጅቱን ከኋላ ሆነው ለማማከርና ለመርዳት እንደሚፈልጉ ነው የሚናገሩት፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ቢተኩም እንኳን ይህንን ሚና ሊጫወቱ እንደሚችሉ ጓዶቻቸው ሳይቀሩ ይመሰክሩላቸዋል፡፡ በሚቀጥሉት ቀናት ውስጥ የሚከናወነው የሥልጣን ሽግግር በእዚህና መሰል ምክንያቶች የሕዝቡንና የዓለም አቀፍ ማኅበረሰቡን ጉጉት እንደሚጨምረው ብዙዎች እምነታቸውን ይገልጻሉ፡፡  
http://www.ethiopianreporter.com

No comments:

Post a Comment