Sunday, September 9, 2012

ዶክተር እሌኒ ከያራ ያገኙትን ሽልማት ለበጐ አድራጐት ድርጅት ማቋቋሚያ ሊያውሉት ነው


የኢትዮጵያ የምርት ገበያ መሥራችና ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶክተር እሌኒ ገብረ መድህን በግብርና ግብዓት አምራችነቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከሚታወቀው ያራ ፋውንዴሽን የዘንድሮ ተሸላሚ በመሆን የተበረከተላቸውን 30 ሺሕ ዶላር ለታዳጊ ሴቶች በጐ አድራጐት ድርጅት ማቋቋሚያ እንደሚያውሉት ገለጹ፡፡

ዶክተር እሌኒ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ 30 ሺሕ ዶላሩን ለታዳጊ ሴቶች ድጋፍ ለማድረግ እንዲወስኑ ያደረጋቸው በአብዛኛው የአገሪቱ ክፍል ታዳጊ ሴቶች ወደ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ሳይሸጋገሩ ትምህርታቸውን የሚያቋርጡባቸው አጋጣሚዎችን በመመልከታቸው ነው፡፡

በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በርካታ ታዳጊ ሴቶች የወንዶችን ያህል ዕድል ኖሯቸው ትምህርታቸውን ለመግፋት ብዙ ሳንካ ያለባቸው በመሆኑ፣ ወደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ሊገቡ ይችሉ የነበሩ ሴቶች ቁጥር እንዲቀንስ የራሱ የሆነ አስተዋፅኦ እንዳለውም ያስታውሳሉ፡፡



ለታዳጊ ሴቶች ሊሰጥ የሚችለውን ድጋፍ በቋሚነት ለማስቀጠልም 30 ሺሕ ዶላሩ እንደመነሻ በማድረግ አንድ የበጐ አድራጐት ማዕከል የሚያቋቁሙ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ማዕከሉም በተመረጡ የክልል ከተሞች ውስጥ ጽሕፈት ቤት ኖሮት የሚሠራ ሲሆን፣ ሥራው በቋሚነት እንዲቀጥል ለማድረግ ደግሞ ሌሎች ዕርዳታ ሰጪና ስፖንሰሮች እንዲካተቱበት ይደረጋልም ብለዋል፡፡

ታዳጊ ሴቶችን ለመርዳት ከዚህ ቀደም በተወሰነ ደረጃም ቢሆን መንቀሳቀሳቸውን ያስታወሱት ዶክተር እሌኒ፣ አሁን የተፈጠረው አጋጣሚ ምኞታቸውን በበለጠ ደረጃ እንደሚያጠናክርላቸው ይናገራሉ፡፡

ከዶክተር እሌኒ ጋር የ2012 የያራ ተሸላሚ የሆኑት የሩዋንዳ የግብርና ሚኒስትር ዶክተር አግነስ ካቢባታ መሆናቸው ያራ ይፋ አድርጓል፡፡

በየዓመቱ በግብርናና ተያያዥ ጉዳዮች ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረጉትን ግለሰቦች የሚሸልመው ያራ፣ ዶክተር እሌኒን ተሸላሚ አድርጐ የመረጠው አነስተኛ ገበሬዎችን ተጠቃሚ የሚያደርገውን ዘመናዊ ገበያ ሥርዓት በመቅረፅና ውጤት በማስገኘታቸው ነው፡፡

በሽልማቱ ዙሪያ ያነጋገርናቸው ዶክተር እሌኒ፣ ያራ የዘንድሮ ተሸላሚ መሆናቸውን ከአንድ ወር በፊት አስታውቋቸው እንደነበርና ሽልማቱ ከፍተኛ ደስታ እንደፈጠረባቸው ገልጸዋል፡፡

ዶክተር እሌኒ የያራን ሽልማት በመስከረም 2005 ዓ.ም. አጋማሽ በታንዛኒያ ርዕሰ ከተማ አሩሻ ውስጥ የሚቀበሉ ሲሆን፣ በሽልማት ሥርዓቱ ላይም የታንዛኒያው ፕሬዚዳንት ጃካያ ኪኪዌቴ፣ የቀድሞ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ ኮፊ አናንና የያራ ፕሬዚዳንት ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ያራ እ.ኤ.አ በ2005 የመጀመሪያውን ሽልማት የሰጠው በቅርቡ ከዚህ ዓለም በሞት ለተለዩት ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ እንደነበር የሚታወቅ ሲሆን፣ አቶ መለስ ባገኙት ሽልማትም ፍሬ አዲስ የተባለና ሴት ተማሪዎችን የሚረዳ በጐ አድራጐት ድርጅት የተቋቋመበት መሆኑ ይታወሳል፡፡

ያራ እስካሁን ሽልማቱን በአብዛኛው የሚያበረክተው የግብርና ዘርፍን በማሳደግ ለተደረገ አስተዋጽኦ ነው፡፡ ዘንድሮ ግን ሽልማቱ ከሚሰጥበት ዋነኛ ዓላማ ወጣ ብሎ የግብርና ምርቶች ገበያ እንዲያገኙ ያስቻሉ ሰዎችን ወደመምረጥና መሸለም መግባቱን ለዶክተር እሌኒ የሰጠው ሽልማት ተጠቃሽ ሆኗል፡፡

ዶክተር እሌኒ የኢትዮጵያ ምርት ገበያን ከመመሥረት አንስቶ በዋና ሥራ አስፈጻሚነት ሲያገለግሉ የቆዩ ሲሆን፣ በመጪው መስከረም 20 ቀን 2005 ዓ.ም. ለአዲሱ ተተኪያቸው በይፋ አስረክበው እስከ ሰኔ 2005 ዓ.ም. የምርት ገበያው ቦርድ አማካሪ ሆነው እንደሚሠሩ መግለጻቸው ይታወሳል፡፡
http://www.ethiopianreporter.com

No comments:

Post a Comment