Wednesday, January 2, 2013

ፕሬዚዳንት ኢሳያስ የኢትዮጵያ መንግሥትን የእንነጋገር ፍላጎት ውድቅ አደረጉ


የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ የኢትዮጵያ መንግሥት በቅርቡ ያቀረበውን የመነጋገር ፍላጎት እንደማይቀበሉ አሳወቁ፡፡

በአሜሪካ የተቀነባበረ ያሉትን በአገራቸው ላይ የተጣለውን የጦር መሣሪያ ዝውውር ማዕቀብም የኤርትራውያንን አንድነት የበለጠ እንዲጠናከር ምክንያት ሆኗል ብለዋል፡፡

ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቅ ይህንን የተናገሩት የአውሮፓውያን አዲስ ዓመት አስመልክተው ሰሞኑን ከኤርትራ ቴሌቪዥን ጋር ባካሄዱት ቃለ ምልልስ ነው፡፡ መንግሥታቸው በአገሪቱ አመጣው ያሉትን ከፍተኛ ልማትና አሜሪካን ጨምሮ ምዕራባዊያን አገራቸውን ለማዳከም ያደረጉትን ጥረት እንዴት እንደተቋቋሙት በዝርዝር አስረድተዋል፡፡



በዚህ በአራት ተከታታይ ክፍለ ጊዜያት የተላለፈው ሰፊ ቃለ ምልልስ፣ ፕሬዚዳንቱ በአሜሪካ መንግሥት ላይ ምርር ያለ ቅሬታ አሰምተዋል፡፡ መንግሥታቸው ክልሉን በተለይ ደግሞ ሶማሊያን ለማተራመስ ባደረገው ጣልቃ ገብነት ምክንያት በኢጋድ ብሎም በአፍሪካ ኅብረት አነሳሽነት በፀጥታው ምክር ቤት ለሁለተኛ ጊዜ የተጣለባቸውን ማዕቀብ፣ የማንም ሳይሆን የአሜሪካ ሴራ መሆኑን አስረድተው፣ ማዕቀቡ ግን በአገራቸው ልማታዊ እንቅስቃሴም ሆነ ዕድገት ላይ ያስከተለው አንድም ጉዳት የለም ብለዋል፡፡ የማዕቀብ ሐሳቡንም ሆነ ሌሎች የሴራ እንቅስቃሴዎች ላለፉት አምስት አሥር ዓመታት የቀጠለ የአሜሪካ የጥላቻ ስትራቴጂ ውጤት መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ዳሩ ግን የኤርትራ ሕዝብ ማዕቀቡን ለመቋቋም ያደረገው ትግል የተሳካ እንደሆነና የሕዝቡንና የአገሪቱ አንድነት በበለጠ እንዲጠናከር ምክንያት ሆኗል ብለዋል፡፡ በአፍሪካ ቀንድ የሚታየው የእርስ በርስ ግጭትና የፖለቲካ ቀውስ የአሜሪካ ስትራቴጂ ውጤት መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ የአካባቢውን ችግር እንደ ክፍተት በመጠቀም በአካባቢው የሚፈልጉት የፖለቲካ ተፅዕኖ ለማሳረፍ በማለት፡፡

በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ከአልጄዚራ ቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፣ አስመራ ድረስም በመሄድ ከፕሬዚዳንት ኢሳያስ ጋር በመነጋገር የሁለቱን አገሮች የድንበር ችግር ለመፍታት ያሳዩትን ፍላጎትም ውድቅ አድርገዋል፡፡ ጋዜጠኛዋ በጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በሞት መለየት ምክንያት ከአዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ወደ ሥልጣን መምጣት ጋር አያይዛ ላነሳችላቸው ጥያቄ ሲመልሱ፣ “ኤርትራ ሥልጣን ላይ ካሉ ግለሰቦች መቀያየር ጋር የምታያይዘው አንዳች ነገር አይኖርም፡፡ ዝንባሌውም ራሱ ከኤርትራ የፖለቲካ ባህልና እሴት የሚቃረን ነው፤” ብለዋል፡፡ ‹‹እነነጋገር የሚለው አባባል ምንጩ ከየት እንደሆነም እንገነዘባለን፤›› ያሉት ፕሬዚዳንት ኢሳያስ፣ ይህ ዓይነት አካሄድ ትኩረት ከማስቀየር በቀር ምንም ዓይነት ጥቅም እንደሌለውና ኤርትራ የምትገባበት ድራማ እንዳልሆነ አመልክተዋል፡፡

ፕሬዚዳንቱ ኤርትራዊያን ወጣቶች አገራቸውን ጥለው ወደ ውጭ እንዲሰደዱ የአሜሪካ የስለላ ድርጅት እየሠራ መሆኑን ገልጸው፣ የኤርትራ ወጣቶች ግን ይህንን ዓላማ የሚያሳኩ አይሆኑም ብለዋል፡፡ በተጨማሪም የድንበር ኮሚሽኑ ውሳኔ ተግባራዊ ላለመሆኑ አሜሪካን ተጠያቂ ያደረጉ ሲሆን፣ በኢትዮጵያ ከፍተኛ የተቃውሞ እንቅስቃሴ እየተካሄደ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
http://www.ethiopianreporter.com

No comments:

Post a Comment