Sunday, July 22, 2012

ንግድ ባንክ የሚድሮክ ኩባንያዎችን በ942 ሚሊዮን ብር ብድር አንበሸበሸ

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለሼክ መሐመድ አል አሙዲ ኩባንያዎች 942 ሚሊዮን ብር ብድር መስጠቱን ምንጮች ገለጹ፡፡ በአቶ በረከት ስምዖን የሚመራው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዳይሬክተሮች ቦርድ ይህንን ብድር ያፀደቀው፣ የሼክ አል አሙዲ ኩባንያ ሚድሮክ ኢትዮጵያ ፕሮጀክት ኦፊስ ለሚገነባው የአፍሪካ ኅብረት ባለአምስት ኮከብ ሆቴል ሕንፃና ለማያ ፒፒ ከረጢት ፋብሪካ ነው፡፡ 

ምንጮች እንደገለጹት፣ ለአፍሪካ ኅብረት ሆቴል ሕንፃ ማጠናቀቂያ 850 ሚሊዮን ብር፣ ለማያ ፒፒ ከረጢት ፋብሪካ ግንባታ ደግሞ 92 ሚሊዮን ብር ነው የባንኩ የዳይሬክተሮች ቦርድ ያፀደቀው፡፡ 

ለብድር ማስመለሻ የተያዙት ዋስትናዎች (ኮላተራል) እየተገነባ ያለው ባለአምስት ኮከብ ሆቴልና የከረጢት ፋብሪካው ናቸው ተብሏል፡፡ 

ሚድሮክ የአፍሪካ ኅብረትን ባለአምስት ኮከብ ሆቴልን ለመገንባት በ1998 ዓ.ም. 90 ሺሕ ካሬ ሜትር ቦታ መረከቡ ይታወሳል፡፡ ሚድሮክ የአዲስ አበባ አስተዳደር ለአፍሪካ ኅብረት የሰጠውን ቦታ ነው የተረከበው፡፡ ኅብረቱ በዚህ ቦታ ላይ ባለአምስት ኮከብ ሆቴል የሚገነባለትን ኩባንያ ለመምረጥ ጨረታ አውጥቶ ነበር፡፡

ሚድሮክ ኮንስትራክሽን እንደ ሌሎች የኮንስትራክሽን ኩባንያዎች ጨረታውን ይወዳደራል ተብሎ ሲጠበቅ፣ ልዩና ያልተጠበቀ ፕሮፖዛል ለኅብረቱ ማቅረቡ ይታወሳል፡፡ 




የሚድሮክ ፕሮፖዛል የሚለው የአፍሪካ ኅብረት ቦታውን በሚድሮክ ስም ቢያዛውር ሚድሮክ በራሱ ወጪ ሆቴሉን እንደሚገነባና ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት እንደሚሰጥ የሚገልጽ ነው፡፡ ኅብረቱ ያወጣውን ጨረታውን በመሰረዝ የሚድሮክን ፕሮፖዛል ተቀብሎ ቦታውን በስሙ ያዛወረለት ሲሆን፣ የአዲስ አበባ አስተዳደር ሊዝ ቢሮ የመሬት ዝውውሩን አፅድቋል፡፡ ባለፈው ዓመት ይህ ቦታ ለሴኪዩሪቲና ለፓርኪንግ አገልግሎት አይበቃኝም ያለው ሚድሮክ ተጨማሪ 17 ሺሕ ካሬ ሜትር ቦታ አስተዳደሩን ጠይቆ ተፈቅዶለታል፡፡

በአሁኑ ወቅት የሆቴሉ ግንባታ በሚድሮክ ኢትዮጵያ ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት እየተካሄደ ነው፡፡ ንግድ ባንክ የሰጠው ብድር ለሆቴሉ ማጠናቀቂያ ሥራዎች የሚውል ነው ተብሏል፡፡ ሌላኛው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የብድር ተጠቃሚ ማያ ፒፒ ከረጢት ፋብሪካ ነው፡፡ ይህ ፋብሪካ በአቶ ኃይሌ አሰግዴ በሚመራው ደርባ ሚድሮክ ሥር ራሱን ችሎ የተቋቋመ ነው፡፡ ዓላማውም በደርባ ሚድሮክ ሥር ያሉት ደርባ ሲሚንቶ ፋብሪካና ሳዑዲ ስታር ግብርና ልማት ድርጅት የሚያመርቱትን ሲሚንቶና ሩዝ ማሸጊያ ከረጢት ለማምረት ነው፡፡ 

ፋብሪካው በኦሮሚያ ክልል ደርባ አካባቢ በ13 ሔክታር መሬት ላይ በመገንባት ላይ ነው፡፡ ፋብሪካው በዓመት 80 ሚሊዮን ከረጢት የማምረት አቅም እንዳለው ይናገራል፡፡ 

በመላ አገሪቱ በጥልቀት በመግባት 538 ቅርንጫፎች የከፈተው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሼክ አል አሙዲ ኩባንያዎች ደንበኛ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከመንግሥት ፕሮጀክቶች ቀጥሎ ለሼክ አል አሙዲ ኩባንያዎች ከፍተኛ ገንዘብ በብድር እያቀረበ መሆኑ ይታወቃል፡፡  

http://www.ethiopianreporter.com

No comments:

Post a Comment