Wednesday, October 5, 2011

ዓይኖቿ የጠፉት ሆስተስ ጤና በአስጊ ሁኔታ ላይ ነው ተባለ


 ‹‹እግዚአብሔር ጤናዋን ሰጥቷት የምትለውን ከሰማሁ በኋላ የምናገረው አለኝ››  ተጠርጣሪና የቀድሞ ባለቤቷ

በተጠርጣሪና የቀድሞ ባለቤቷ መስከረም 2 ቀን 2004 ዓ.ም ሌሊት ሁለት ዓይኖቿ የጠፉት የኢትዮጵያ አየር መንገድ የበረራ አስተናጋጅ የነበረችው የዋና አስተናጋጅ አበራሽ ኃይላይ የጤና ሁኔታ በአስጊ ደረጃ ላይ መሆኑን ፖሊስ ለፍርድ ቤት አስታወቀ፡፡
ፖሊስ የሆስቴሷ ጤና በአስጊ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ያስታወቀው፣ በትናንትናው ዕለት ለአዲስ አበባ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ቦሌ ምድብ ችሎት በተጠርጣሪው ላይ ቀርቦ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ በጠየቀበት ወቅት ነው፡፡

ፖሊስ ለፍርድ ቤት እንደገለጸው፣ ተጎጂዋ ያለችው ከኢትዮጵያ ውጭ ባንኮክ በሕክምና ላይ ነው፡፡ በደረሰው መረጃና ከዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል ባገኘነው የሕክምና ማስረጃ መሠረት ጤናዋ አደጋ ውስጥ ነው፡፡

በትናንትናው ዕለት የዋለው ችሎት ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት ይጀመራል በሚል ፍርድ ቤቱ ማስተናገድ ከሚችለው በላይ በርካታ ሰዎች የተገኙ ቢሆንም፣ ችሎቱ የተጀመረው ከጠዋቱ 5፡15 ሰዓት ላይ ነበር፡፡ በቦሌ ክፍለ ከተማ ሴቶች፣ ሕፃናትና ወጣቶች ጽሕፈት ቤት አስተባባሪነት ‹‹አሁን በዓይኔ መጣህ፣ እየተስፋፋ ያለው የሴቶች ጥቃት ይቁም›› የሚሉ መፈክሮችን ይዘው በክፍለ ከተማው ውስጥ የሚገኙ ከ14 ወረዳዎች የተሰባሰቡ በርካታ ሴቶች በፍርድ ቤቱ ቅጥር ግቢ ከጠዋቱ 2፡30 ሰዓት ጀምሮ ተሰልፈው ችሎቱን ሲጠባበቁ ቆይተዋል፡፡

ሙሉ ጥቁር የለበሱ የተጎጂዋ ቤተሰቦች፣ የቅርብ ዘመዶች፣ የሥራ ዩኒፎርማቸውን የለበሱ ጥቂት የበረራ አስተናጋጆች፣ እናቶችና ወጣቶች ተሰልፈው የችሎቱን መጀመር ሲጠባበቁ፣ የአበራሽ አጎት አቶ አስመላሽ ሞላ ሁለት ዓይኖቿ ተጎልጉለው ወጥተውና የላይና የታችኛው የዓይኖቿ ክፍሎች ተቆርጠው ከውስጥ የሚወጣው ደም ወደ ጎንጮቿ ሲፈስ የሚያሳየውን ፎቶ ሲያወጡ ግቢው በዋይታና ለቅሶ ተናወጠ፡፡

መገናኛ ከሚገኘው መንገድና ትራንስፖርት ቢሮ በስተቀኝ በኩል በውኃና ፍሳሽ ባለሥልጣንን አልፎ በነገው ሰው ትምህርት ቤት ፊት ለፊት በሚያስገባው ጠባብ አስፓልት 50 ሜትር እንደተሄደ፣ በስተግራ በኩል ኮከብ ኮሌጅ ቅጥር ግቢ ውስጥ የሚገኘው የቦሌ ምድብ ችሎት ውስጥ የተሰበሰቡት የችሎቱ ታዳሚዎች ፎቶውን እያዩ መጮህና መላቀሳቸውን ቀጠሉ፡፡

‹‹አፋጣኝ ፍትሕ ይሰጠን›› እና ሌሎች ድርጊቱን የሚቃወሙ መፈክሮችን በማሰማት ቁጭት በተሞላበት ሁኔታ የተሰበሰቡት የችሎቱ ታዳሚዎች በማጉረምረም ላይ እያሉ፣ በአዲስ አበባ ፖሊስ የታጀበው ተጠርጣሪ በላንድክሩዘር ከፍርድ ቤቱ ቅጥር ግቢ ሲደርስ፣ ግቢው በከፍተኛ ጩኸትና ሁከት ተተራመሰ፡፡

ፊቱን ጭምብል መሳይ መሸፈኛና በጃኬት ኮፍያ ሸፍኖ ግራና ቀኝ እጁን በፖሊስ የተያዘው ተጠርጣሪ ፍስሐ ታደሰ፣ ዙሪያዋን በችሎት ታዳሚ ተጠቅጥቃ ከዳኛው ፊት ለፊት ለእሱ መቆሚያ በተተወች ጠባብ ቦታ ላይ ገብቶ ቆመ፡፡

ተጠርጣሪውና ዳኛው ወደ ችሎት ከመግባታቸው በፊት በችሎት ሥነ ሥርዓት አስከባሪዎችና በፖሊስ አባላት ‹‹ትረብሹና፣ ድምፅ ታወጡና ቅጣት ይጠብቃችኋል፤›› በማለት በተደጋጋሚ ፍተሻ ሲካሄድባቸው የቆዩት የችሎቱ ታዳሚዎች፣ ተጠርጣሪው ሲገባ ከጉንጭ ያላለፈ ማጉረምረማቸውን አልተውም ነበር፡፡

በተጣበበችው ክፍል ውስጥ ግራና ቀኝ በተከበበው የዳኛው መግቢያ በር ወደ ችሎቱ የዘለቁት ዳኛ አርአያ ኃይለ ማርያም፣ የመጀመሪያ ጥያቄያቸው ፖሊስ ተጠርጣሪውን አዘግይቶ (5፡15 ሰዓት) ያቀረበበትን ምክንያት እንዲያስረዳ ነው፡፡

‹‹እንደሚታወቀው የመኪና እጥረት አለብን፡፡ እስረኞችን የምናቀርበውም ከየካና ከቂርቆስ ፖሊስ ጣቢያዎች በመሆኑ ጊዜ ይወስድብናል፡፡ ቢሆንም ስለሰዓቱ መርፈድ ፍርድ ቤቱን ይቅርታ እንጠይቃለን፤›› በማለት የቦሌ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምርያ ወንጀል ምርመራ ባልደረባ ሳጅን ታምሩ አበበ ምላሽ ሰጡ፡፡

በመቀጠልም ባለፈው ቀጠሮ ምርመራ አጠናቀው እንደሚያቀርቡ የገለጹ ቢሆንም፣ አሁንም እንዳልተጠናቀቀላቸው በመግለጽ፣ የጠየቁት ተጨማሪ የጊዜ ቀጠሮ እንዲፈቀድላቸው በድጋሜ ጠየቁ፡፡

ለምን ተጨማሪ የጊዜ ቀጠሮ እንደሚፈቀድላቸው በድጋሚ እንዲያስረዱ ፍርድ ቤቱ ሲጠይቃቸው፣ ተጠርጣሪው በዋስ ቢለቀቅ በተለያየ መንገድ ከአገር ሊወጣ ስለሚችል፣ ተጨማሪ የሰዎች ማስረጃዎችን መሰብሰብ ስለሚቀራቸውና የተጎጂዋ የውጭ አገር የምርመራ ውጤት እስከሚመጣ ጊዜ ሊወስድ ስለሚችል መሆኑን መርማሪው ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡

ፖሊስ ተጠርጣሪው ድርጊቱን የፈጸመበት ስለትና የድርጊቱን ሁኔታ የሚያሳይ የፎቶ ሰነድ ለፍርድ ቤቱ አሳይቶ የተጠርጣሪውን የዋስትና ጥያቄ ተቃውሟል፡፡

ፍርድ ቤቱ የፖሊስን ቃል ከሰማ በኋላ የተጠርጣሪውን ሁለት ጠበቆች አስተያየት እንዲሰጡ ሲጠይቃቸው፣ ‹‹ማንም ተጠርጣሪ በፖሊስ ጣቢያ ሊታሰር የሚችለው ለተወሰነ ጊዜ ነው፡፡ ከዚያ በላይ ሊታሰር አይችልም፡፡ ፖሊስ እስካሁን ምን እያደረገ ነው? በውጭ ጉዳይ ሚነስቴር በኩልም ቢሆን ያለውን ኃይልና ዘዴ ተጠቅሞ የተጎጂዋ የምርመራ ውጤት የሚመጣበትን መንገድ ማመቻቸት አለበት፤›› ብለዋል፡፡

የተጎጂዋ ሕይወት አደጋ ላይ ነው ስለሚባለው ጉዳይ፣ በማስረጃ ያልቀረበ በመሆኑ ተቀባይነት እንደማይኖረው የገለጹት የተጠርጣሪው ጠበቆች፣ ፖሊስ በሙሉ ኃይሉ ተጠቅሞና ምርመራውን በአስቸኳይ አጠናቆ ክስ እንዲመሠረት ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው ጠይቀዋል፡፡

ተጠርጣሪው የሚለው ካለ ፍርድ ቤቱ ጠይቆት፣ ‹‹ከጠበቃ ጋር በግልጽ መነጋገር አልቻልኩም፡፡ የራሴን ፍላጎትና ሐሳብ ማስተላለፍ አልቻልኩም፡፡ በእሷ ጉዳይ ላይ እግዚአብሔር ጤናዋን ሰጥቷት እሷ የምትለውን ሰምቼ የምለው አለኝ፤›› ሲል ታዳሚው በከፍተኛ ሁኔታ የማጉረምረም ድምፅ አሰምቶ ሲጨርስ፣ ንግግሩን ቀጥሎ  ‹‹እስከዚያው ድረስ በማረፊያ ቤት ብቆይም ግዴለም፤›› ብሏል፡፡

ፍርድ ቤቱ የፍትሕ ሒደቱ እንዲፋጠን እያደረገ መሆኑን ጠቁሞ፣ ፖሊስ ምርመራውን በተፋጠነ መንገድ እንዲጨርስ ተጠርጣሪው በሕጉና በሕገ መንግሥቱ ድንጋጌ መሠረት ነፃ ሆኖ የመታየት መብቱ የተከበረ በመሆኑ፣ የሕግ አማካሪዎቹን በአግባቡ እንዲያገኝ እንዲደረግ አዟል፡፡

የተጠርጣሪው ጠበቃ ተጠርጣሪውን ለማነጋገር ወደ ታሰረበት ጣቢያ ሲሄዱ ማነጋገር የምትችሉት፣ ‹‹አንድ ፖሊስ ከእናንተ ጋር ተቀምጦ እያዳመጠ መሆን አለበት፤›› መባላቸውን ለፍርድ ቤቱ ገልጸው፣ በነፃነት የሕግ ዕርዳታ አገልግሎት ሊሰጡት አለመቻላቸውንም ለፍርድ ቤቱ አመልክተዋል፡፡

ሌላው ጠበቃው ያነሱት ነጥብና ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ እንሰዲሰጥላቸው የጠየቁት፣ በሕዝቡ ዘንድ በተጠርጣሪው ላይ ቀድሞ ፍርድ እየተሰጠ መሆኑንና አንዳንድ ሚዲያዎችም አላስፈላጊ መረጃ እያስተላለፉ መሆኑን በመግለጽ ነው፡፡

ፍርድ ቤቱ ፖሊስ የጠየቀውን የ14 ቀናት ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ፈቅዶ፣ ለጥቅምት 7 ቀን 2004 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ከሰጠ በኋላ፣ ሕዝቡ በሕግ ያልተፈረደበትን ተጠርጣሪ ነፃ ሆኖ የመገመት መብቱን ማሳጣት እንደሌለበት በመናገር፣ አላግባብ ይዘግቡ የነበሩ ሚዲያዎች እንደነበሩ በማረጋገጥ የሚመለከተውን አካል መጠየቅ የሚችል መሆኑን በመጠቆም ችሎቱ ተጠናቋል፡፡

ችሎቱ ተጠናቆ ተጠርጣሪው ሲወጣ የችሎቱ ታዳሚዎች ከፍተኛ የተቃውሞ ጩኸትና የተለያዩ መፈክሮችን ከ30 ደቂቃ በላይ በማሰማት የፍርድ ቤቱን ቅጥር ግቢ ለቀው ወጥተዋል፡፡

No comments:

Post a Comment