Monday, August 4, 2014

ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን በአመፅ ለመናድ በማሴር የተጠረጠሩ የህትመት ውጤት አሳታሚዎችና ድርጅቶች ተከሰሱ

አዲስ አበባ፣ ሀምሌ 28፣ 2006 (ኤፍ.ቢ.ሲ.)  ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን በአመፅ ለመናድ በማሴር የተጠረጠሩ የህትመት ውጤት አሳታሚዎችና ድርጅቶች ተከሰሱ።

የፍትህ ሚኒስቴር ዛሬ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት በላከው መግለጫ ላይ እንዳስታወቀው፥ በየጊዜው ህገ መንግስቱንና ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን በሀይል ለመናድ የአመፅ ቅስቀሳና የሀሰት ወሬዎችን በመንዛት ህገ መንግስታዊ ስርዓቱ በሀይል እንዲፈረስ  እና ህዝብ በመንግስት ላይ ያለአግባብ አመኔታ እንዲያጣ የሚያደርጉ የወንጀል ተግባራትን በመፈፀም ተጠርጥረው የተከሰሱት ፋክት፣ ጃኖ፣ ሎሚ፣ አዲስ ጉዳይ እና እንቁ የሚባሉ መፅሄቶችና አፍሮ ታይምስ የሚባል ጋዜጣ አሳታሚዎችና ድርጅቶች ናቸው።

ሚኒስቴሩ የህግ የበላይነትን የማስከበር ሀላፊነት ያለበት መንግስት ከክስ መለስ የተሻሉ ናቸው ያላቸውን አማራጮች አሟጦ በመጠቀም ህትመቶቹ ምግባራቸውን እንዲያርቁ ለማድረግ ያላሰለሰ  ጥረት ማድረጉን አንስቷል።

ሆኖም አንዳንድ የህትመት ውጤቶች የመንግስትን ቻይነት ከመጤፍ ባለመቁጠር የፈፀሙትን የህግ ጥሰት አባብሰው መቀጠላቸውን መግለጫው ይጠቅሳል።


ከህገ መንግስቱና  ህገ መንግስቱን ለማስፈፀም በወጡ ህጎች የተበጁ ገደቦችን በማክበር ነፃነቱን ለመጠቀምና ተግባራዊ ለማድረግ የሚንቀሳቀሱ በርካታ ሀላፊነት የሚሰማቸው የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎችና ድርጅቶች እንዳሉ ነው መግለጫው የጠቀሰው።

በአንፃሩ በህገ መንግስቱ የተበጁትን ገደቦች በማን አለበኝነት በመጣስ ስራዬ ብለው ብሄራዊ ደህንነትን አደጋ ላይ በሚጥል መልክ አመፅና ሁከትን የሚቀሰቅሱ፣ አክራሪነትንና  ሽብርተኝነትን የሚያወድሱ እንዲሁም የሚያበረታቱ፣ በህዝቡ መሃከል የዘርና የሃይማኖት ጥላቻን የሚቀሰቅሱ፣ የህዝብ መሪዎችንና የተቋማትን መልካም ስምና ዝና  በሀሰት የሚያጠፉና የሚወነጅሉ  አንዳንድ ህትመቶች እንዳሉም አስታውቋል።

ሚኒስቴሩ እንዳለው መንግስት በነፃ ሀሳብን የመግለፅ መብትን በማበረታታት የመገናኛ ብዙሃን በተለይም የግሉ የህትመት ውጤቶች በዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ተተኪ የሌለውን ገንቢ ሚናቸውን በሀላፊነት ስሜት እንዲወጡ ለማስቻል  ከባለድርሻ አካላት ጋር  የምክክር መድረኮችን አዘጋጅቷል።

እያደገ ያለውን የህትመት ኢንዱስትሪ ልማት ለማጎልበት በማሰብ በህትመት ሚዲያው ዘርፍ የሚታዩ አንዳንድ ፅንፍ የወጡ ግድፈቶችን በህጋዊና አስተዳደራዊ እርምጃ ከማረም ተቆጥቦ ሁኔታውን በሆደ ሰፊነት ሲከታተልና የህትመት ሚዲያው ማህበረሰብ ችግሮቹን ለመቅረፍ የእርምት እርምጃዎችን እንዲወስድ በተደጋጋሚ ሲያሳስብ መቆየቱን ነው የፍትህ ሚኒስቴር ያስታወቀው።

የጥቃታቸው ሰለባ የሆነው ህዝብም በእነዚህ የህትመት ውጤቶች የህግ ከለላ በተሰጣቸው ጥቅሞቹ ላይ ያለማቋረጥ የሚደርሰውን ጥሰት ለማስቆም መንግስት ህጋዊ እርምጃ እንዲወስድ በተለያዩ መንገዶች ሲጠይቅ መቆየቱን አስታውሷል መግለጫው።

የህትመት ውጤቶቹ ከዚህ ተግባራቸው እንዲቆጠቡ የተሰጣቸውን ማሳሰቢያ ወደጎን በመተዋቸው ተከሰዋል ብሏል።

ክስ የማቅረቡ ሂደትም በማን አለብኝነት በተደጋጋሚ ህጉን በጣሱ እና በሚጥሱ አሳታሚዎችና የመገናኛ ብዙሃን ድርጅቶች ላይ እንደሚቀጥልም አስታውቋል።

በአገሪቱ በ2006 በአማካይ 21 ጋዜጦች እና 48 መፅሄቶች በስርጭት ላይ ይገኛሉ።
http://www.fanabc.com

No comments:

Post a Comment