Saturday, August 2, 2014

ታዳጊ ብሔራዊ ቡድን ቅዳሜ ዋናው እሑድ ከሜዳቸው ውጪ ይጫወታሉ

-እነሳላዲንና ጌታነህ አልተካተቱም

ከሳምንት በፊት የጋቦን አቻውን በአዲስ አበባ ስታዲየም አስተናግዶ ያለግብ የተለያየው ዕድሜያቸው ከ17 ዓመት በታች የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለመልሱ ጨዋታ ነገ ሐሙስ ወደ ጋቦን ያመራል፣ ቅዳሜ ይጫወታል፡፡

በሚቀጥለው ዓመት ሞሮኮ ለምታስተናግደው የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ በጳጉሜን አልጄሪያን በሜዳው የሚያስተናግደው ዋናው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በበኩሉ፣ እሑድ ከአንጎላ ጋር ለሚያደርገው የወዳጅነት ጨዋታ ዛሬ ምሽት ወደ ሥፍራው ያመራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በቀጣይም በብራዚል ከተለያዩ ክለቦች ጋር ተመሳሳይ የወዳጅነት ጨዋታ ለማድረግ ከአንጎላ መልስ ወደ ብራዚል ለመጓዝ ዝግጅት እያደረገ መሆኑ ፌዴሬሽኑ አስታውቋል፡፡

ለአገሪቱ እግር ኳስ ትንሣኤ በመፍትሔ ሰጪነት ከሚጠቀሱ በርካታ ነጥቦች  ታዳጊ ወጣቶች ላይ መሥራት አንዱና ብቸኛው መንገድ ሆኖ ቢቆይም ተግባራዊ ሳይሆን ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ባለፈው መስከረም መጨረሻ የብሔራዊ ፌዴሬሽኑን የአመራር ኃላፊነት የተረከበው ሥራ አስፈጻሚ ይህንኑ ለዓመታት የዘለቀ እንቆቅልሽ መፍታት ይችል ዘንድ በታዳጊ ወጣቶች ላይ ተስፋ የሚያጭር እንቅስቃሴ ማድረግ ጀምሯል፡፡ የስፖርቱ ቤተሰብና ሙያተኞችም ይኸው ተስፋ ሰጪ ጅምር ተጠናክሮ እንዲቀጥል በመጠየቅ ላይ ይገኛሉ፡፡ በተለይ በየዓመቱ ለተጨዋቾች ዝውውር በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ እያፈሰሱ የሚገኙት ክለቦች ከሁሉ በፊት ለታዳጊ ወጣቶች ልዩ ትኩረት እንዲሰጡ ይጠይቃሉ፡፡


አዲሱ የፌዴሬሽኑ አመራር ምንም እንኳ ከጅምሩ ከዕድሜ ጋር የተያያዙ ችግሮች ቢኖሩበትም፣ በአዲስ አበባ የሚገኙ ሰባት የፕሪሚየር ሊግ ክለቦች ዕድሜያቸው ከ17 ዓመት በታች ቡድኖችን እንዲያቋቁሙ አድርጎ ውድድሩን በበላይነት ሲመራ ቆይቷል፡፡ በሚቀጥለው ዓመት በኒጀር ለሚካሄደው ዕድሜያቸው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ታዳጊዎች እግር ኳስ ዋንጫ ላይ አገሪቱ መሳተፍ ትችል ዘንድ የታዳጊዎች ብሔራዊ ቡድን አዘጋጅቶ የማጣሪያ ጨዋታውን ጀምሯል፡፡ ቡድኑም  ከሳምንት በፊት በአዲስ አበባ ስታዲየም የጋቦን አቻውን አስተናግዶ 0 ለ0 የተለያየበት ተጠቃሽ ነው፡፡  ታዳጊዎቹ ምንም እንኳ በልምድ ማነስ ምክንያት በተጋጣሚያቸው ላይ ጎል የማስቆጠር ችግር ቢስተዋልባቸውም በእንቅስቃሴያቸው ግን የስፖርት ቤተሰቡን ትኩረት ያገኙበት አጋጣሚ ታይቷል፡፡

በሌላ በኩል፣ ዋናው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በሚቀጥለው ዓመት ሞሮኮ  ለምታስተናግደው የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ቅድመ ዝግጅት እንዲረዳው የወዳጅነት ጨዋታ ጥያቄዎች እየቀረቡለት ይገኛል፡፡

ከኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ሕዝብ ግንኙነት ክፍል እንደደረሰን መረጃ ከሆነ፣ በፖርቱጋላዊው ማሪያኖ ባሬቶ እየተዘጋጀ የሚገኘው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከአንጎላ አቻው በተደረገለት ጥሪ መሠረት የወዳጅነት ጨዋታ ለማድረግ በዛሬው ዕለት ወደ ሥፍራው አምርቷል፡፡ ጨዋታው በዓለም አቀፉ እግር ኳስ ማኅበር (ፊፋ) ዕውቅና ያለው ጨዋታ ሲሆን፣ እሑድ ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ብሔራዊ ቡድኑ ከአንጎላው የወዳጅነት ጨዋታ በኋላ፣ በብራዚል ከአምስት የተለያዩ ክለቦች ጋር ተመሳሳይ የወዳጅነት ጨዋታ ለማድረግ ወደ ብራዚል ያመራል ተብሎ እንደሚጠበቅም የፌዴሬሽኑ ሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ወንድምኩን አላዩ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ ወጪውን በተመለከተ ኃላፊው፣ የአንጎላውን ጨምሮ ከትራንስፖርት በስተቀር የተቀረው በአስተናጋጆቹ ይሸፈናል ተብሏል፡፡

ፖርቱጋላዊው የዋልያዎቹ አሠልጣኝ እሑድ ለሚያደርጉት ጨዋታ የ23 ተጨዋቾችን ዝርዝር ይፋ አድርገዋል፡፡ ከነባሮቹ የቡድኑ ተጨዋቾች ሳላዲን ሰይድ፣ ጌታነህ ከበደ፣ አሉላ ግርማና ምንያህል ተሾመ በዝርዝሩ አልተካተቱም፡፡

የተመረጡት ተጨዋቾች መሱድ መሐመድ፣ አንዳርጋቸው ይሳቅ፣ ቶክ ጀምስ፣ ሽመልስ ተገኝ፣ ጀማል ጣሰው፣ አበባው ቡጣቆ፣ ታደለ መንገሻ፣ ብርሃኑ  ቦጋለ፣ ምንተስኖት አዳነ፣ አክሊሉ አየነው፣ ኤፍሬም አሻሞ፣ ሲሳይ ባንጫ፣ ዳዋ ሁጤሳ፣ ጋቾች ጋኖም፣ ግርማ በቀለ፣ አዳነ ግርማ፣ በኃይሉ አሰፋ፣ ፍፁም ገብረማርያም፣ ናትናኤል ዘለቀ፣ ፍቅሩ ተፈራ፣ ሽመልስ በቀለ፣ ቤርጌቾና አሥራት መገርሳ ናቸው፡፡
http://www.ethiopianreporter.com/

No comments:

Post a Comment