Wednesday, September 18, 2013

ዎልማርት የኢትዮጵያ ንግድ ኢንተርፕራይዝን ሊያስተዳድር ነው

በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 235/2005 መሠረት ከወራት በፊት የተቋቋመውና በመላ አገሪቱ የተደራጀ የሸቀጦች ንግድ አገልግሎት ለመስጠት የተዘጋጀውን የኢትዮጵያ ንግድ ኢንተርፕራይዝ፣ በሁለት ዓመታት የማኔጅመንት ኮንትራት ለማስተዳደር በዓለም አቀፍ ደረጃ ግዙፍ የሆነው የአሜሪካው ዎልማርት ኩባንያ ስምምነት ለማድረግ መዘጋጀቱን ምንጮች ገለጹ፡፡

ዎልማርት የተባለው ኩባንያ ከሰሐራ በታች በሚገኙ 12 የአፍሪካ አገሮች ቅርንጫፎችን በመክፈት የተለያዩ ሸቀጦችን ለተጠቃሚዎች በጅምላና በችርቻሮ በማቅረብ ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ሸማቾችንና የአገሪቱን ኢኮኖሚ በመፈተን ላይ የሚገኘውን የዋጋ ግሽበት በማጤን፣ የኢትዮጵያ ገበያ ውስጥ የመግባት ፍላጐቱን በማሳየት ከመንግሥት ጋር ሲደራደር ቆይቷል፡፡


ይሁን እንጂ ዎልማርት በሚገኝባቸው አገሮች የሚያደርገው የንግድ እንቅስቃሴን የተገነዘበው መንግሥት ኩባንያው ያለ ቅድመ ዝግጅት ወደ ኢትዮጵያ እንዲገባ አልፈለገም፡፡ ይልቁንም በአነስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኙ የአገር ውስጥ የንግድ ድርጅቶችን መግደል ይሆናል በሚል ግምገማ፣ ፈቃድ እንደነፈገው ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑ አንድ የመንግሥት ባለሥልጣን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

የመሠረታዊ ፍጆታ ሸቀጦችን ከውጭ በማስገባትና የኢትዮጵያ የጅምላ ንግድ አገልግሎት ድርጅትን በማጠናከር የዋጋ ግሽበቱን ለመቆጣጠር የአጭር ጊዜ አማራጭ መፍትሔ ሆኖ እንዲሠራ በመ
ንግሥት በኩል መወሰኑን ምንጮች አስረድተዋል፡፡

በዚህ ሁኔታ መቀጠል ዘለቄታዊ መፍትሔ የሚያመጣ ባለመሆኑና የአገር ውስጥ የንግድ ድርጅቶች ጉዳት ሳይደርስባቸው የዋጋ ግሽበቱን መከላከል የሚያስችል የንግድ ኢንተርፕራይዝ በመንግሥት ባለቤትነት እንዲቋቋም መወሰኑን ባለሥልጣኑ ገልጸዋል፡፡ በዚህም መሠረት በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ከአራት ወራት በፊት የኢትዮጵያ ንግድ ኢንተርፕራይዝ መቋቋሙን አስረድተዋል፡፡

ኢንተርፕራይዙ በአንድ ቢሊዮን ብር ካፒታል እንዲቋቋም በአዋጁ የተወሰነ ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ 250 ሚሊዮን ብሩ የተከፈለ ካፒታል መሆኑን አስረድተዋል፡፡ የኢንተርፕራይዙ አደረጃጀት ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ እንዲሆን በመፈለጉ፣ አደረጃጀቱን በተመለከተ የጀርመኑ ኤቲ ኪርኒ የተባለ ኩባንያ ተቀጥሮ በማማከር ላይ እንደሚገኝ ምንጮች ገልጸዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት የኢንተርፕራይዙ አደረጃጀት ከሞላ ጐደል መጠናቀቁን የሚገልጹት ምንጮች፣ ከሁለት ወራት በኋላ ኢንተርፕራይዙ አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምር ተናግረዋል፡፡ ኢንተርፕራይዙ በ26 የአገሪቱ ከተሞች ቅርንጫፎችን እንደሚኖሩትና በአገሪቱ ከዚህ ቀደም ያልነበረ ግዙፍ የጅምላና የችርቻሮ የሸቀጦች ንግድ ድርጅት እንደሚሆን ገልጸዋል፡፡

ይህንን ግዙፍ ኢንተርፕራይዝ በሚፈለገው ዓለም አቀፍ የአገልግሎት አሰጣጥ ደረጃ ለማስተዳደር የአገር ውስጥ ልምድና አቅም ባለመኖሩ፣ ከዚህ ቀደም በኢትዮጵያ ቅርንጫፉን ለመክፈት ጥያቄ አቅርቦ የነበረው ግዙፉ ዎልማርት ኩባንያ ኢንተርፕራይዙን በኮንትራት እንዲያስተዳድር ጥያቄ ቀርቦለት፣ ላለፉት በርካታ ወራት ከንግድ ሚኒስቴር ጋር በድርድር ላይ እንደነበር ታውቀዋል፡፡

ኩባንያው በኢትዮጵያ ንግድ ኢንተርፕራይዝ ላይ የአክሲዮን ድርሻ እንዲኖረው ጠይቆ እንደነበር የገለጹት ኃላፊው፣ ይህ ጥያቄ በመንግሥት በኩል ተቀባይነት እንዳላገኘ ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ድርድሩ መጠናቀቁንና ኩባንያውም ፈቃደኛ በመሆኑ በቀሪዎቹ ሦስት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ስምምነት ይፈጽማል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል፡፡ በሌላ በኩል ጅንአድ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ከሚገኙ መጋዘኖቹ መካከል የተወሰኑትን ለአዲሱ ኢንተርፕራይዝ እንዲለቅ መወሰኑን ምንጮች ገልጸዋል፡፡

ዎልማርት ኩባንያ በዓለም ላይ ግዙፍ ከሚባሉት የሸቀጣ ሸቀጥ ንግድ ድርጅቶች መካከል ግንባር ቀደሙ ነው፡፡ እ.ኤ.አ. በ2011 ጠቅላላ ገቢው 447 ቢሊዮን ዶላር የነበረ ሲሆን፣ ትርፉ 15.7 ቢሊዮን እንደነበር መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
http://www.ethiopianreporter.com

No comments:

Post a Comment